tg-me.com/Nolawii/3926
Last Update:
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (17)
13. ንግግርህ ብቁ ይሁን (ለ)
1. አዳምጥ
ጥሩ ተናጋሪ ጥሩ አድማጭ ፣ ጥሩ ፀሐፊ ጥሩ አንባቢ ነው ። ሰውዬው ራሱን በልቶት እግሩን ብታክለት ከማስደሰት ይልቅ ታሳምመዋለህ ። ሳያዳምጡ መናገርም እንዲሁ ነው ። ማዳመጥ ሰዎችን ለመረዳትና ለመርዳት ጥልቅ ፍላጎት ማሳየት ነው ። ያልተረዳኸውን ሰው መርዳት አትችልም ። ሰዎች ከእርዳታ ይልቅ አሳባቸውን የሚረዳላቸው/የሚያውቅላቸው ሰው ይፈልጋሉ ። ብዙ ሰው ከአእምሮ ሕመሙ የሚድነው ስታዳምጠው ነው ። አዳምጠህ ስትናገር ርእስ ትጠብቃለህ ፣ ያንን ሰው ትማርከዋለህ ። ደግሞም የመጨረሻው ይጸናልና ኋላ መናገር መልካም ነው ።
2. ንግግር አታቋርጥ
ሰው አሳቡን መጨረስ አለበት ። ምንም ቢናገር ዓመት አያወራም ። ስለዚህ ንግግሩን አስጨርሰው ። አሳቡ እንዳይጠፋህ ማስታወሻ ያዝ ። የሰው ልጅ አስተማማኝ ሰላም እንዳለው ምልክቱ ታግሦ መስማት ሲችል ነው ። ለአንድ ሰዓት ስብከት የሚሰሙ ሰዎች አንድ ነገር አላቸው ። እርሱም የውስጥ ሰላም ነው ። እግዚአብሔርን የሚያህል ትልቅ አምላክ የሚሰማው ነውና ሰውን ለማዳመጥ አትፈተን ። የተጨነቁ ሰዎች ትልቁ ችግራቸው የሚሰማቸው ሰው ማጣት ነው ። በትክክል እንደ ሰማሃቸው ካወቁ ምንም ምክር ሳትሰጣቸው ይፈወሳሉ ። ማዳመጥም አገልግሎት ነው ። ጆሮውን ላልነፈገን ጌታ ውለታው የተጨነቁትን መስማት ነው ።
3. በአሉታዊ ንግግር አትጀምር
ሰዎችን ከጉድለታቸው ተነሥተህ ስታወራቸው ዋጋ የላችሁም እያልካቸው ይመስላቸዋል ። ዋጋ የለህም ያልከው ዋጋህን ያሳጣሃል ። እግዚአብሔር ሲናገር ሁልጊዜ ከመልካሙ ጀምሮ ነው ። ሙሴን አንተ ገዳይ አላለውም ፣ ነጻ አውጪ አለው ። ጌዴዎን የፈሪዎች ሊቀ መንበር ቢሆንም አንተ ጎበዝ አለው ። የሞተውን የናይን መበለት ልጅ አንተ ሬሳ ሳይሆን “አንተ ጎበዝ” አለው ። ሬሳን “አንተ ጎበዝ” የሚል የእኔ መድኃኔ ዓለም ብቻ ነው ። ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት መልእክት ሲላክ ካላቸው ጥሩ ነገር ተነሥቶ የሌላቸውን ይናገራቸዋል (ዘጸ. 3 ፡ 10 ፤ መሳ. 6 ፡ 12 ፤ ሉቃ. 7 ፡ 14 ፤ ራእ. 2 ፡ 2-7) ። በንግግር መነሻ ላይ ከጉድለት መጀመር ግንኙነትን በዜሮ ማባዛት ነው ። ሰዎች የሚጠሉት ዋጋ የላችሁም የሚል ድምፅን ነው ። የምትነቅፋቸው ሊያጠፉህ ይችላሉና ተጠንቀቅ ። ከትዳር አጋር ጋር የማትግባቡት ከጉድለት ስለምትጀምሩ ነው ። ሰይጣን በወኪል ሳይሆን በቀጥታ የሚዋጋህ “ዋጋ የለህም” በሚል ድምፅ ነው ። ሰው ራሱን የሚያጠፋው የራሱ ዋጋ ሲወርድበት ነው ። “ብኖርም ብሞትም የምጠቅምና የማጎዳ ሰው አይደለሁም” ሲል በራሱ ላይ ይጨክናል ።
ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 22 ቀን 2016 ዓ.ም.
BY Nolawi ኖላዊ
Warning: Undefined variable $i in /var/www/tg-me/post.php on line 280
Share with your friend now:
tg-me.com/Nolawii/3926