tg-me.com/deacongirmayeshitla/8210
Last Update:
🕊
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡
[ † ግንቦት ፲፫ [ 13 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት † ]
† 🕊 ቅዱስ አርሳኒ 🕊 †
ቅድስት ሃይማኖት እዚህ ዛሬ እኛ ጋር የደረሰችው በበርካታ ሰማዕታትና ጻድቃን ደም ነው:: ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግድግዳዎቿ እንጨትና ድንጋይ እንዳይመስሏችሁ:: አጽመ ቅዱሳን ነው እንጂ::
ቅዱሳን ልዑለ ባሕርይ ክርስቶስን እንደ እኔ እና እንደ ዘመኑ ትውልድ በከንፈራቸው የሚሸነግሉ አልነበሩም:: እነርሱ በፍጹም ልባቸው ስለ ፍቅሩ ሕይወታቸውን አሳልፈው ሰጡ እንጂ:: በቅድስናቸው ከተመሰከረላቸው ቀደምት ቅዱሳን አንዱ ደግም ቅዱስ አርሳንዮስ ነው::
ቅዱሱ የተወለደው በ፫፻፵፭ [ 345 ] ዓ/ም ሮም ውስጥ ነው:: በወጣትነቱ ይሕ ቀረህ የማይሉት የጥበብና የፍልስፍና ሰው ነበር:: በተለይ በትልቁ የሮም ቄሳር ቴዎዶስዮስ ዘመን በቤተ መንግስት አካባቢ የተከበረና የንጉሡ ልጆች መምሕር ነበር:: አኖሬዎስና አርቃዴዎስን ቀጥቶ ያሳደጋቸውም እርሱ ነበር::
በድንግልና እስከ ፵ [ 40 ] ዓመቱ ድረስ ሮም ውስጥ ቆየ:: ከዚህ በኋላ ግን ስለ ሰማያዊ ነገሮች ሲያስብ መልዐኩ በሕልም ወደ ግብፅ ሒድ አለው:: በመጀመሪያ ወደ እስክንድርያ ቀጥሎ ወደ ገዳመ አስቄጥስ ሒዶ መነኮሰ:: በቆይታ ግን ብሕትውና ምርጫው ሆነ::
ቅዱስ አርሳኒ በእነዚሕ ነገሮቹ ይታወቃል :-
፩. በምንም ምክንያት ከማንም ጋር አያወራም:: [ለ፷ [60] ዓመታት በአርምሞ ኑሯል]
፪. በቤተ መቅደሱ ግድግዳ ተጠግቶ እንባውን ሲያፈስ የርሱን አካል አርሶ በመሬት ላይ ሲፈስ ይታይ ነበር:: ከእንባው ብዛት ቅንድቦቹ ተላልጠው አልቀው ነበር::
፫. በርካታ ድርሳናትን ደርሷል:: ብዙዎቹ ዛሬም ግብጽ ውስጥ አሉ::
፬. ሸንጎበቱን ወደ ደረቱ አዘንብሎ ስለሚቆም ማንንም ቀና ብሎ አያይም ነበር::
፭. ለጸሎት አመሻሽ ፲፩ ሰዓት [11:00] አካባቢ ላይ ይቆምና ጸሎቱን የሚጨርስ ፀሐይ ግንባሩን ስትመታው ነው::
፮. ሁል ጊዜ ራሱን "አንተ ሰነፍ [ሐካይ] እያለ ይገስጽ ነበር::
፯. በገዳማውያን ታሪክ የርሱን ያሕል በቁመቱ ረዥም አልተገኘም ይባላል:: የራሱ ጸጉር በጀርባው የወረደ ሲሆን ጽሕሙን በስዕሉ ላይ እንደምታዩት ነጭና እስከ መታጠቂያው የወረደ ነበር::
እነዚህ ግን በጣም ጥቂቶቹ ናቸው::
ቅዱስ አርሳንዮስ አካሉ በተጋድሎ ደቆ: ለ፷ [60] ዓመታት በግሩም መንፈሳዊነት ኑሮ በ፻ [100] ዓመቱ በዚሕች ዕለት ዐርፏል::
አምላካችን እግዚአብሔር ከታላቁ የቅድስና ሰው አርሳኒ በረከት አይለየን::
🕊
[ † ግንቦት ፲፫ [ 13 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]
፩. ቅዱስ አርሳንዮስ - አርሳኒ [ጠቢብ ገዳማዊ]
[ † ወርኀዊ በዓላት ]
፩. እግዚአብሔር አብ
፪. ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላዕክት
፫. ፺፱ "99ኙ" ነገደ መላዕክት
፬. ቅዱስ አስከናፍር
፭. ፲፫ " 13ቱ " ግኁሳን አባቶች
፮. አቡነ ዘርዐ ቡሩክ
" የፍጥረት ወገን ሁሉ በሰው ይገራል:: ደግሞ ተገርቷል:: ነገር ግን አንደበትን ሊገራ ማንም ሰው አይችልም:: የሚገድል መርዝ የሞላበት ወላዋይ ክፋት ነው:: በእርሱ ጌታንና አብን እንባርካለን:: በእርሱም እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠሩትን ሰዎች እንረግማለን:: ከአንድ አፍ በረከትና መርገም ይወጣሉ:: ወንድሞቼ ሆይ ይህ እንዲህ ሊሆን አይገባም:: " [ያዕ.፫፥፯-፲፩] (3:7-11)
† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †
[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ]
† † †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖 🕊 💖
BY ዲያቆን ወልደ ሰንበት መጣጥፎች ፣ ትምህርቶች
Warning: Undefined variable $i in /var/www/tg-me/post.php on line 280
Share with your friend now:
tg-me.com/deacongirmayeshitla/8210