tg-me.com/heppymuslim29/6448
Last Update:
ዲኔ ላይ ደህና ነኝ፡፡ መልክ አለኝ ባይባልም አልከፋም፡፡ በባህሪዬ ጥሩ ነኝ ብዬ አስባለሁ፡፡ ከቤተሰብ ሳልርቅ ነው ያደግኩት፡፡ የልጅነት ጊዜዬ አልፎ ወጣትነት መጣ፡፡ እንደማንኛዋም ሴት ትዳር አሰብኩ፡፡ ግና በማላውቀው ምክንያት ድርሻዬ ዘገየብኝ፡፡ ለጋብቻ የሚጠይቀኝ ጠፋ፡፡ ከኔ በኋላ የተወለዱ የቤተሰብም፣ የዘመድም፣ የሰፈርም ልጆች አንድ በአንድ አገቡ፡፡ ወለዱ፡፡ ልጆቻቸዉም አደጉ፡፡ ሳላስበው 34 ዓመት ሆነኝ፡፡ ዕድሜዬን ሳስታውሰው ደነገጥኩ፡፡ ብቻዬን ቆሜ የቀረሁ እስኪመስለኝ ድረስ ተሠማኝ፡፡
፨፨፨
የሆነ ጊዜ ከቅርብ ዘመድ የሆነ አንድ ወጣት ለጋብቻ ጠየቀኝ፡፡ ፈቃደኝነቴን ገለጽኩ፡፡ ሁለት ዓመት ይበልጠኛል፡፡ ዲኑም ፀባዩም ቆንጆ ነው፡፡ ደስ አለኝ፡፡ ከሀሳቤ የተገላገልኩ መሰለኝ፡፡ ቤተሰብም ደስ አለው፡፡
.
ኒካሕ ለማሰር ተዘጋጀን፡፡ አንዳንድ ጉዳዮችን ለመጨረስ ብሎ መታወቂያዬን ይዞ ሄደ፡፡
.
.ከሁለት ቀን በኋላ ስልክ ተደወለልኝ፡፡ እናቱ ነበረች፡፡ እንደምትፈልገኝ ነገረችኝ፡፡ ምን ይሆን ብዬ እየበረርኩ ሄደኩኝ፡፡ ቤታቸው ገባሁ፡፡ ጥቂት ካወራን በኋላ መታወቂያዬን እያሳየችኝ እዚህ ላይ የተጠቀሰው የትውልድ ቀኔ ትክክል ስለመሆኑ ጠየቀችኝ፡፡ አዎን ትክክል ነው አልኳት፡ እንግዲያዉስ አንች አርባ ተጠግተሸል መውለድ አትችይም፡፡ አለችኝ፡፡ 34 ዓመቴ እኮ ነው እንዴት አልችልም አልኳት፡፡ አይ … አንች ሰላሳ አልፎሻል እኔ ደግሞ ልጅ አይደለም ገና የልጅ ልጅ ማየት እፈልጋለሁ አለች፡፡ ጋብቻው እንዲሰረዝ ሞገተች፡፡ ልጇንም አሳመነች ለቤተሰቤ ምን እንደምላቸው እያሰላሰልኩ ተስፋ ቆርጬ ወደቤቴ ተመለስኩ፡፡
፨፨
ቀናት አለፉ፡፡ ድፍን ስድስት ወራትን በሐዘን አሳለፍኩ፡፡ ረጃጅም ቀንና ሌሊቶችን ስብሰለሰል ከረምኩ፡፡ በር በሩን ባይ እኔን ብሎ የሚመጣ ለኔ የተፃፈ ባል ጠፋ፡፡ ብቸኝነት፣ ባይተዋርነት፣ አጥንት ድረስ ዘልቆ ተሰማኝ፡፡አባቴ ሁኔታዬን ይከታተላል፡፡ ስለኔ አብዝቶ ተጨነቀ፡፡ በመጨረሻም ከወንድሜ ጋር ለዑምራ እንድሄድ መከረኝ፡፡ ሂጂና በተከበረው የአላህ ቤት አጠገብ ብሶትሽን ተናገሪ፤ የዉስጥሽን የዉስጥ አዋቂ ለሆነ ጌታ ተንፍሺ አለኝ፡፡
ዑምራ ሄድኩኝ፡፡ የአላህ ቤት ከዕባ ፊት ቁጭ ብዬ ረጅም ዱዓ አደረግኩ፡፡ ለርሱ የዉስጥ ስሜቴን ሁሉ አንሾካሸኩ፡፡ አለቀስኩ፤ ፈረጄን ያቀርብልኝ ዘንድ ተማፀንኩት፡፡
፨፨
የሆነ ቀን ሱንና ከሰገድኩ በኋላ ጥቂት ቁጭ አልኩ፡፡ ከኋላዬ አንዲት ሴት ባማረ ድምጽ ቁርኣንን ታነባለች፡፡ “የአላህ ችሮታ ብዙ ነው፡፡” የሚል ትርጉም ያለዉን የቁርኣን አንቀጽ ስታነብ ቀልቤ በተለየ መልኩ ወደዚያ ተሳበ፡፡ በቁርኣን ዉስጥ የዚህ ዓይነት አንቀጽ ስለመኖሩ ገረመኝ፡፡ አላህ በችሮታው ያስበኝ ዘንድ ተማፀንኩት፡፡ሴትዮዋ አየችኝ፡፡ ምን እንደሆንኩ ጠየቀችኝ፡፡ ሁኔታዬን ነገርኳት፡፡ አብሽሪ አለችኝ “ አብሽሪ አላህም ያሰብሽዉን ይሠጥሻል፤ ኢንሻአላህ ደስም ይልሻል፡፡” አለችኝ፡፡
፨፨
ዑምራውን አጠናቅቄ ተመለስኩ፡፡ ድንገት የረጅም ጊዜ ጓደኛዬንና ባሏን በዐይሮፕላን ማረፊያው አገኘኋቸው፡፡ የባሏን ጓደኛ ለመቀበል እየጠበቁ ነበር፡፡ ሰላምታ አቅርቤላቸው ትንሽ እንዳወጋን ጓደኛቸው ደረሰና ተሰነባበትን፡፡ ወዲያው አባቴ ደርሶ ተቀበለኝ፡፡
፨፨
ጥቂት ቀናት አለፉ፡፡ አሁን ከበፊቱ በተሻለ ልቤ በመጠኑ ሰክኗል፡፡ ዱዓዬን አላቋረጥኩም፡፡
የሆነ ቀን ያች ጓደኛዬ ደወለችልኝ፡፡ ያን ቀን ያየኝ የባሏ ጓደኛ ለትዳር እንዳሰበኝ ነገረችኝ፡፡ በአንድ ቀን እይታ እንዴት ሊሆን ይችላል ብዬ ተገረምኩ፡፡ ግና ለአላህ ምን ይሳነዋል!!፡፡
በእውነቱ የማይታሰብ ነገር ሆነብኝ፤ ማመን አቃተኝ፡፡ እሱ ግን የምሩን ነበር፡፡ ስለኔ ሁሉን ነገር ከጓደኛዬ ከሰማ በኋላ አላንገራገረም፡፡ ወደ ቤተሰቦቼ ሽማግሌ ላከ፡፡ ደስ አለኝ፡፡ ተስፋዬ ለመለመ፡፡ ወዜ ተመለሰ፡፡ ስሜቴ ታደሰ፡፡
፨፨
በመጨረሻም አገባሁ፡፡ ጥሩ አፍቃሪ፣ መልካምና ደጋፊ፣ አዛኝና አሳቢ ባል … አላህ ሠጠኝ፡፡ ለኔም ለወላጆቹም ጥሩ ሰው ነበር፡፡
.
ካገባሁ ቀናት ሄዱ፣ ሁለትና ሦስት ወራት ተተኩ፡፡ ሌላ ሀሳብ አስጨነቀኝ፡፡ የእርግዝና ምልክት ናፈቀኝ፡፡ ግና እስካሁን ምንም አላስተዋልኩም፡፡ ሲበዛ አሳሰበኝ፡፡ እንቅልፍ አጣሁ፡፡
.
መመርመር እንደምፈልግ ለባሌ ነገርኩት፡፡ ወደ ሀኪም ቤት ሄድን፡፡ ጥቂት ቆይተን ለዉጤቱ ተጠራን፡፡ ልቤ መምታቱን ጨመረ፡፡ ገና እንደገባሁ “መዳም መብሩክ!” አለችኝ ሀኪሟ፡፡
አርግዤ ነበር፡፡ ሱብሐነላህ!፡፡ ለዚህ ብስራት ነበር እንዴ አላህ እዚህ ድረስ ያመጣኝ አልኩ፡፡
.
የእርግዝና ጊዜዬ ሰላማዊ ነበር፡፡ ግና የዕድሜዬ መግፋት መጠነኛ ተጽእኖ ነበረው፡፡ ሆዴ እያደገ ሲመጣ ሰዉነቴ ከበደኝ፡፡ እንደምንም የድካሙ ወራት አለፈ፡፡ የምጡ ቀን ደረሰ፡፡ በቀዶ ጥገና ነበር የወለድኩት፡፡ ከተሠጠኝ ሰመመን ስነቃ ቤተሰቦቼና ባለቤቴ ዙርያዬ ተሰብስበዋል፡፡ ይስቃሉ፣ ይጫወታሉ፡፡ “ምን ወለድኩ?” አልኳቸው ያለሁበትን ሁኔታ እያስታወስኩ፡፡
.
የተመካከሩ ነበር የሚመስለው፡፡ አንድ ላይ ሆነው ነበር ሰርፕራይዝ ያደረጉኝ “ወንድ እና ሴት!” አሉኝ፡፡ መንታ!!፡፡ የኔን መንቃት ሲጠብቅ የነበረው ባሌ በደስታ ተፍነከነከ፡፡ እኔንም ሀሴት የምሆነውን አሳጣኝ፡፡ ብችል ተነስቼ በዘለልኩ፡፡ ቁስሌ ገና እርጥብ ነው፡፡ ሱጁድም ራቀኝ፡፡ በተኛሁበት እንባዬ በሁለቱም ጉንጮቼ በኩል ዝምብሎ ሲፈስ ይታወቀኛል፡፡ በትኩስ እንባ ፊቴ ታጠበ፡፡ ምስጋናዬን ያወጣሁበት ቃል እሱ ነበር፡፡
ያቺ “አላህ ያሰብሽዉን ይሠጥሻል፤ ኢንሻአላህ ደስ ይልሻል፡፡” ያለችኝ ሴት ትዝ አለችኝ፡፡
፨፨፨
“ወለሰውፈ ዩዕጢከ ረቡከ ፈተርዷ” የሚለዉን የቁርኣን አንቀጽ አስታወስኩ፡፡ ስለ አላህ አስብኩና በሀሳብ ርቄ ሄድኩ፡፡ የሱ ሥራ አብዝቶ ገረመኝ፡፡ እኛ ተስፋ እንቆርጣለን እንጂ እሱ ያዘጋጀልን ነገር አለ፡፡ እኛው ሁለት ልብ ሆነን ተቸገርን እንጂ በርግጠኝነት በአንድ ሆነን ልብ ይሠጠናል ብለን ብንለምነው ይሠጠናል፡፡
እኛው እንቸኩላለን እንጂ እሱ ለሁሉም ነገር መላና መፍትሄ አለው፤ ለሁሉም ነገር ምክንያትና ጊዜ አለው፡፡ ለአላህ ዉሳኔ መታገስና ፈረጃዉን መጠበቅ ትልቅ ዒባዳ ነው፡፡
፧
እንኳን እኛ ነቢዩ ዘከርያም በልጅ እጦት ተፈትነዋል፡፡ “ጌታዬ ሆይ ብቻዬን አትተወኝ፡፡ …” ሲሉ ነበር ዱዓ ያደረጉት፡፡
ኢንሻአላህ ፈጣሪሽ ያሰብሽዉን ይሠጥሻል፤ አንቺም አንድ ቀን ደስ ይልሻል፡፡
፨፨፨፨፨፨፨
“ቂሰሱን ሚነል ዋቂዕ” ከተሠኘ መጽሐፍ የተወሰደ፡፡
@heppymuslim29
BY HAppy Mûslimah
Warning: Undefined variable $i in /var/www/tg-me/post.php on line 280
Share with your friend now:
tg-me.com/heppymuslim29/6448