tg-me.com/mnenteyiklo/2814
Last Update:
"ያመነ የተጠመቀም ይድናል" ተብሏልና "ያመነ" ብሎ ስለሚጀምር እምነት ይቀድማል ከዚያም ጥምቀት ይከተላል የሚሉ ሕፃናትም ለማመን አልበቁምና ማጥመቅ አይገባም የሚሉ አሉ፦
[የሕጻናት ጥምቀት- Paedobaptism]
👉 በመጀመርያ በራሳቸው ቅደም ተከተል አበጅተው እምነት ይቀድማል ካሉ በማቴ 28:19 ላይ "እንግዲህ ሂዱ አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኀቸው ያዘዝኀችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኀቸው ደቀ መዛሙርቴ አድርጓቸው፡፡" ላይ እያጠመቃችኀቸው ካለ በኋላ ነውና አስተምሩ የሚለው እዚህ ላይ ደግሞ ጥምቀት ሲቀድም እንመለከታለን፡፡ ታድያ መጽሐፍ ቅዱስ ርስ በርሱ ይጣረሳል? አይደለም። መጽሐፍ ቅዱስን ለራስ እንዲመች አድርጎ የመጥቀስ ስህተት የፈጠረው እንጂ። ለማመን ያልደረሱ ህፃናት በቤተሰብ እምነት ይጠመቃሉ፡፡ በቤተ ክርስቲያንም ነገረ ሐይማኖትን እንዲያውቁ በመንፈሳዊ ጉዞ በክርስትና ሕይወት እንዲጓዙ ሲባል ኃላፊነት የሚወስድ የክርስትና አባት [God father] ይሰጣል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ እንደምንመለከተው እምነት ተሸጋጋሪ ነው፡፡ የአባት እምነት ለልጅ ሲጠቅም እንመለከታለን፡፡ ለዚህም የመቶ አለቃውና (ማቴ 8:8-10ን ተመልከቱ) የከነናዊቷን ሴት ታሪክ (ማቴ 15:22-28ን ተመልከቱ) ማስታወስ ይበቃል፡፡ በአባት እምነት ልጁ ሲድን ሲፈወስ እንመለከታለን፡፡ በከነናዊቷ ሴትም እምነት ልጇ ስትድን እንመለከታለን፡፡ በአንዱ እምነት ሌላው ሲፈወስ ሲድን እንመለከታለን፡፡ እምነት ተሸጋጋሪ ነውና፡፡ [መርሐ ጽድቅ ባሕለ ኃይማኖት፤ ሊቀ መዘምራን ሞገስ ዕቁበ ጊዮርጊስ] ስለዚህ በቤተሰብ እምነት ልጅን ማጥመቅ ይገባል፡፡
ጌታ በወንጌል ለኒቆዲሞስ " ሰው ዳግመኛ ከካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግስት ሊያይ አይችልም" ዮሐ 3:3 ብሎታል። በጥምቀት ዳግም መወለድ ለድኅነት ያስፈልጋል፡፡ ድኅነት ደግሞ ለአዋቂ ብቻ የተሰጠ ሳይሆን ለህፃናትም ጭምር ነው እንጂ፡፡
👉 በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ
- በሐዋ 16 :15 "እርሷም ከቤተሰቦቿ ጋር ከተጠመቀች በኋላ..."
- ሐዋ 16:33 "ያን ጊዜም እርሱ ከቤተሰቦቹ ጋር ተጠመቀ" ልድያ ከቤተሰቦቿ ጋር እንደተጠመቀች: የወኅኒ ጠባቂውም ከነቤተሰቦቹ እንደተጠመቀ ይነግረናል፡፡ ህፃናት ደግሞ የቤተሰብ አካል ናቸው፡፡ "ከነቤተሰቦቹ" ተባለ እንጂ ከህፃናት በቀር አልተባለም፡፡ ይህም የህፃናትን ጥምቀት እንዲገባ ያስተምረናል፡፡
👉 በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ከአብርሃም ጋር ቃል ኪዳን በገባው መሰረት የእግዚአብሔር ሕዝብ የሚባሉት ይገዘሩ ነበር። ግዝረቱም በተወለዱ በ8ኛው ቀን ይፈጸማል። ምንም የማያውቁት ሕጻናት ተገዝረው የእግዚአብሔር ወገን መሆንን ያገኛሉ አይከለከሉምም። ይህ ግዝረት ለጥምቀት ምሳሌ ነው። ቆላ.2:11-12:: ስለዚህ ለማመን ያልደረሱትን ሕጻናትን ማጥመቅ ይገባል። እስራኤል ዘሥጋ ባሕሩ ተከፍሎላቸው የመሻገራቸው ነገር የጥምቀት ምሳሌ ነው። 1ኛ ቆሮ 10:2። ባሕሩ ተከፍሎላቸው የተሻገሩት አዋቂዎች ብቻ አልነበሩም ሕጻናትም ነበሩ። በምሳሌው ይህን ከተማርን በአማናዊው ጥምቀት ደግሞ ሕጻናትን ጭምር ማጥመቅ እንደሚገባ ያስተምረናል።
ተክለ ማርያም [ጅማ ሐመረ ኖኅ ኪዳነ ምሕረት]
ይቀጥላል...
BY ምን እንጠይቅሎ?
Warning: Undefined variable $i in /var/www/tg-me/post.php on line 280
Share with your friend now:
tg-me.com/mnenteyiklo/2814