Telegram Group Search
+ መርጦ መወለድ +

ከእገሌ ልወለድ ብሎ መርጦ የተወለደ የለም:: ምረጡ ብንባል ምን ዓይነት ወላጅ እንመርጣለን? ቀድመን የመገምገም ዕድል ቢኖረን ምን ዓይነት ወላጆች እንመርጣለን። መቼም በወላጆቼ ደስተኛ ነኝ የሚል ሰው "እኔ ደግሜም ብወለድ ከአባዬ ከእማዬ ነው መወለድ የምፈልገው" ማለቱ አይቀርም። ግን ደግሞ ዕድሉን ቢያገኝ መቼም ትንሽም ቢሆን የሚያስተካክለው ነገር አይጠፋም። መርጦ መወለድ አይቻልም እንጂ ቢቻል የምንመርጠው ልዩ ምርጫ ይሆናል።

መርጦ የተወለደ ክርስቶስ ብቻ ነው። በምድር ወደሚኖሩት ሁሉ ተመልክቶ መዓዛዋን መርጦ ፣ በቅድስናዋ ውበት ተማርኮ ከእርስዋ ሊወለድ የመረጣት የተመረጠች እናት ድንግል ማርያም ብቻ ናት። የፈጣሪ ምርጫ እንደ ሰው አይደለም። ሰው ፊትን ያያል እርሱ ግን እስከ ልብ ድረስ ዘልቆ ይመለከታል። እንዴት ብትነጻ ፣ እንዴት ብትቀደስ ነው? እስከ ውስጥዋ ዘልቆ አይቶ ከእርስዋ ሊወለድ የመረጣት? ንጉሥ ውበትዋን የወደደላት ፣ ለእናትነት የመረጣት ቅድስት እንዴት የከበረች ናት?
አዎ መርጦ የተወለደ የለም ፣ ክርስቶስ ግን መርጦ ብቻ ሳይሆን ፈጥሮ የተወለደ ነው። መቅደሱን አንጾ የገባባት እርሱ ነው። መርጦ ለተወለደብሽ ለአንቺ በጸጒራችን ቁጥር ምስጋና እናቀርባለን።

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መስከረም 21 2012 ዓ ም
የግሸንዋን ንግሥት በረከት በመናፈቅ
ሜልበርን አውስትራሊያ
+ ረቢ ወዴት ትኖራለህ? +

ከመጥምቁ ዮሐንስ ተማሪዎች መካከል ሁለቱ "የእግዚአብሔር በግ እነሆ" የሚለውን የመምህራቸውን ስብከት ሰምተው ጌታን ተከተሉት::

"ኢየሱስም ዘወር ብሎ ሲከተሉትም አይቶ፦ ምን ትፈልጋላችሁ? አላቸው። እነርሱም፦ ረቢ፥ ወዴት ትኖራለህ? አሉት፤ መጥታችሁ እዩ፡ አላቸው። መጥተው የሚኖርበትን አዩ፥ በዚያም ቀን በእርሱ ዘንድ ዋሉ፤ አሥር ሰዓት ያህል ነበረ" ዮሐ. 1:37-39

ጌታን ተከትለው የሚኖርበትን ካዩት ደቀ መዛሙርት አንደኛው ስም እንድርያስ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የራሱን ስም በወንጌሉ ላይ እኔ የማይጽፈውና ቤተ ክርስቲያን ግን የራሱን ነገር ሲገልፅ በሚጠቀመው ቋንቋ የምታውቀው ወንጌላዊው ዮሐንስ ነበረ::

"ረቢ፥ ወዴት ትኖራለህ? አሉት፤ መጥታችሁ እዩ፡ አላቸው። መጥተው የሚኖርበትን አዩ" የሚለው ቃል በእርግጥ በጣም አስገራሚ ነው:: የክርስቶስን መኖሪያ ማየት መፈለጋቸው ፈልገው እንዳያጡት አድራሻውን ለማወቅ ካላቸው ጉጉት የተነሣ ነበረ::
ሆኖም ክርስቶስ በምድር ላይ ሲኖር ቋሚ አድራሻ አልነበረውም:: ራሱ እንደተናገረ :-ለቀበሮዎች ጉድጓድ ለሰማይም ወፎች መሳፈሪያ አላቸው፥ ለሰው ልጅ ግን ራሱን የሚያስጠጋበት የለውም" (ማቴ. 8:20)

እነዚህ ሁለት ደቀ መዛሙርት የጠየቁት "ረቢ፥ ወዴት ትኖራለህ?" የሚለው ጥያቄ አድራሻ ከመጠየቅ ከፍ ያለ ጥልቅ ጥያቄ ነው:: ነቢያቱ "የጥበብ ሀገርዋ ወዴት ነው? ማደሪያዋስ ወዴት ነው?" ብለው የተጨነቁለት የጥበብ ክርስቶስ ማደሪያ የት እንደሆነ ማወቅ የነፍስ ዕረፍት ነውና ተራ ጥያቄ አይደለም?
ይህ ጥያቄ ዳዊት ለዓይኖቹ እንቅልፍ ለሽፋሽፍቶቹ ዕረፍት ያልሠጠበት "የያዕቆብ አምላክን ማደሪያ እስኪያገኝ ድረስ" የለመነበት ጥያቄ ነው::

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? የሚለው ጥያቄ እንድርያስና ዮሐንስ በአንድ ቀን ብቻ የሚመለስ ጥያቄ መስሎአቸው አብረውት ሔደው አብረውት ዋሉ እንጂ የጌታ መኖሪያ ግን ያን ቀን የዋለበት ብቻ አይደለም::

ረቢ ወዴት ትኖራለህ?
"ብርሃንህንና እውነትህን ላክ፤ እነርሱ ይምሩኝ፥ ወደ ቅድስናህ ተራራና ወደ ማደሪያህ ይውሰዱኝ" መዝ. 43:3

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? "ወደ ሰማይ ብወጣ፥ አንተ በዚያ ነህ፤ ወደ ሲኦልም ብወርድ፥ በዚያ አለህ። እንደ ንስር የንጋትን ክንፍ ብወስድ፥ እስከ ባሕር መጨረሻም ብበርር፥ በዚያ እጅህ ትመራኛለች፥ ቀኝህም ትይዘኛለች" መዝ. 139:8 ለአድራሻ የሚያስቸግረው የረቢ መኖሪያው ብዙ ስለሆነ የት ትኖራለህ ለሚለው ጥያቄ መልሱ "መጥታችሁ እዩ" ብቻ ነው::

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? ብለው ለጠየቁት ደቀ መዛሙርቱ ቦታውን ከመናገር ይልቅ "መጥታችሁ እዩ" ያለው ጌታ እርሱን ጸንተው እስከተከተሉ ድረስ በሕይወታቸው ዘመን ሁሉ አልፎም ከሞቱ በኋላ የሚያዩት ብዙ መኖሪያ ስላለው ነበር::

የረቢ መኖሪያው ብዙ ነው:: "የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል፡ ወደ እርሱም እንመጣለን፡ በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን" እንዳለ ቃሉን የሚጠብቅ ሰው ሰውነትም የእርሱ ማደሪያ ነው:: (ዮሐ. 14:23)

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? " በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ፤ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበር፤ ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና" ስትል ሰምተንህ ነበር:: (ዮሐ. 14:2) የአንተ መኖሪያ መንግሥተ ሰማያት አይደለምን? ቅዱስ ጳውሎስ "ልሔድ ከክርስቶስ ጋር ልኖር እናፍቃለሁ" ሲል እንደሰማነው እስከ ዐሥር ሰዓት ድረስ እንደመዋል ዐሥሩ መዓርጋት ላይ የደረሱ በጽድቅ መንገድ የሔዱ የሚያዩት ማደሪያህ መንግሥተ ሰማያት አይደለምን? መጥተን ለማየት "እናንተ የአባቴ ቡሩካን ወደ እኔ ኑ" እስክትለን በተስፋ እየጠበቅን አይደለምን?

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? ካሉት ጠያቂዎች መካከል አንዱ ዮሐንስ መሆኑን ሳስብ ደግሞ ዮሐንስ ያያቸው የረቢ መኖሪያዎች ከገሊላ እስከ ታቦር ተራራ ፣ ከሊቶስጥራ እስከ ቀራንዮ ፣ ከወንጌል እስከ ራእይ እጅግ ብዙ እንደነበሩ ታየኝ::

"ወዴት ትኖራለህ?" ብሎ ጠይቆ ጌታን የተከተለው ዮሐንስ "መጥተህ እይ" በተባለው መሠረት የጌታን መኖሪያ የእርሱን ያህል ያየም ሰው የለም::

ዮሐንስ "ረቢ ወዴት ትኖራለህ?" ለሚል ጥያቄው ግን አንጀት የሚያርስ ልብ የሚያሳርፍ መልስ ያገኘው አርብ ዕለት መስቀሉ ሥር ነበር:: ወዴት ትኖራለህ? ላለው ዮሐንስ የዘጠኝ ወር ከተማውን የዘላለም ማረፊያውን "እነኋት እናትህ" ብሎ ሲሠጠው መጥቶ ካያቸው የረቢ መኖሪያዎች ሁሉ የምትበልጠውን መኖሪያ አየ:: "እግዚአብሔር ጽዮንን መርጦአታልና፥ ማደሪያውም ትሆነው ዘንድ ወድዶአታልና፥ እንዲህ ብሎ፦ ይህች ለዘላለም ማረፊያዬ ናት፤ መርጫታለሁና በዚህች አድራለሁ" ብሎ የመረጣትን ማደሪያ ከማየት በላይ ምን ክብር አለ? (መዝ. 132:13)

ዮሐንስ ይህችን የረቢ መኖሪያ ወዲያው ወደ ቤቱ ወሰዳት:: ዮሴፍ ሊወስዳት ስላልፈራ ምን እንዳገኘ ያውቃልና እርሱም ይህችን የዕንቁ ሳጥን ወደ ቤቱ ወስዶ ቢዝቁት የማያልቅ ጸጋን ተጎናጸፈ::

ጌታ እናቱን ለዮሐንስ መሥጠቱ የሁለት ድንግልናዎች ማስረጃ ሆነ:: የድንግል ማርያም ዘላለማዊ ድንግልናም የዮሐንስ ድንግልናም በጌታ ንግግር ታወቀ::

አንዳንዶች እንደሚመስላቸው ድንግል ማርያም ከጌታ ሌላ ልጆች ቢኖሩአት ኖሮ "እናቴን ከልጆችዋ ነጥለህ ወደ ቤትህ ውሰዳት" "አንቺም ልጆችሽን ይዘሽ ወደ ሰው ቤት ሒጂ" ብሎ ለዮሐንስ አይሠጣትም ነበር:: ድንግል ማርያም የአብን አንድያ ልጅ አንድያ ልጅዋ አድርጋለችና አምላክ ባደረበት ዙፋን ሌላ ፍጡር ያላስቀመጠች የአምላክ ብቸኛ ዙፋን ፣ እግዚአብሔርን አስገብታ በርዋን የዘጋች ዘላለማዊት ድንግል መሆንዋ ለዮሐንስ በመሠጠትዋ ታወቀ:: ዮሐንስም ቤት ንብረት የሌለው መናኝ ባይሆንና ሚስት ድስት ያለው ሰው ቢሆን ድንገት ወደ ቤቱ ይዞአት እንዲሔድ እናቱን ባልሠጠው ነበር::

የሰው ልጅ ድኅነት ታሪክ በሁለት "እነሆ"ዎች መሃል መከናወኑ እጅግ ይደንቃል:: የሰው መዳን የተጀመረው "እነሆኝ የጌታ ባሪያ" ብላ ራስዋን ለፈጣሪ በሠጠችው ድንግል ቃል ሲሆን የተጠናቀቀው ደግሞ "እነኋት እናትህ" ብሎ በደም በታጠበ አንደበቱ በነገረን የኑዛዜ ቃል ነው::

ረቢ ወዴት ትኖራለህ? ለእኛም አታሳየን ይሆን? እስከ ዐሥር ሰዓት መዋል ፣ ዐሠርቱን ትእዛዛትህን ፣ ዐሥሩን የቅድስና ደረጃዎችን መውጣት ላቃተን ለእኛስ መኖሪያህን ታሳየን ይሆን? መጥታችሁ እዩ የሚለውን ጥሪ ሰምተን ለማምጣት አቅም ላነሰን መጻጉዕዎች ፣ ዓይን ላጣን በርጤሜዎሶች ተነሡ እዩ ብለህ መኖሪያህን አታሳየን ይሆን? መቅደስህን እንመለከት ዘንድ ፣ መኖሪያህን መንግሥትህን እናያት ዘንድ ፣ ዮሐንስ ያያትን መኖሪያህ እናትህን እናይ ዘንድ እንመኛለን::

ረቢ ወዴት ትኖራለህ?

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መስከረም 21 2016 ዓ.ም.
ለእመብዙኃን ዝክር የተጻፈ

"ንዒ ማርያም ለዕውር ብርሃኑ
ወንዒ ድንግል ለጽሙዕ አንቅዕተ ወይኑ
ኦ ኦ ተኃድግኒኑ ኦ ኦ ትመንንኒኑ
ኀዘነ ልብየ እነግር ለመኑ"
ወተዘከርኒ ለኃጥእ ገብርኪ ተክለ ማርያም
"እግዚአብሔር ብፈቅድ ብንኖርም ይህን ወይም ያን እናደርጋለን"

ባሕርያት (Elements) ለዚህ ዘመን ክርስቲያን ወጣቶች የተበረከተ እጅግ ውብ የሥነ ጽሑፍ ሥራ ነው:: ይህ ውድ መጽሐፍ አምስት ቅጽ ያላቸው እጅግ የተዋቡ መጻሕፍት ውሕድ ሲሆን በዘመናዊው ዓለም እግዚአብሔርን በመምሰል ሕይወትን እንዴት መለማመድ እንደሚቻል የሚያሳይ በዳያስፖራነት የተወለዱ ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ሕይወት የለወጠ እና በብዙ ሺህዎች ኮፒ የተሸጠ መጽሐፍ ነው::

የዚህን መጽሐፍ የመጀመሪያ ቅጽ በእግዚአብሔር ፈቃድ ወደ አማርኛ የተረጎምሁት ሲሆን እስከ ኅዳር ማርያም የአርታኢያንን ዱላ ቀምሶ በኅትመት ቤት አልፎ ከእጃችሁ ይገባል:: የቀሩትም መጻሕፍት በወራት ልዩነት ውስጥ ይከተላሉ::

N.B. የዛሬ ዓመት ገደማ ሊወጣ መንገድ ጀምሮ የነበረው "ሉተርና ሚካኤል" የተሰኘ መጽሐፍ በታላላቅ አባቶቼና ወንድሞቼ በሳል ምክር ምክንያት ከይዘቱ የተነሣ የሚወጣበትን ምቹ ጊዜ እየጠበቀና ተከድኖ እየበሰለ ያለ መሆኑን እገልጻለሁ::

"ነገር ግን በክርስቶስ ሁልጊዜ ድል በመንሣቱ ለሚያዞረን በእኛም በየስፍራው ሁሉ የእውቀቱን ሽታ ለሚገልጥ ለአምላክ ምስጋና ይሁን" 2ኛ ቆሮ. 2:14
+ አባቶቻችን እንዲህ አሉ +

"እሳትና ውኃን ማዋሐድ እንደማይቻል በሌሎች ኃጢአት መፍረድም በራስ ኃጢአት ከመጸጸት ጋር አብሮ አይሔድም" ቅዱስ ዮሐንስ ዘሰዋስው

"የማያማትብ እጅ ቀኙም ግራውም አንድ ነው" አባ ፓስዮስ ዘደብረ አቶስ

"እግዚአብሔር ለኃጢአተኛ ሰው ያለው ፍቅር
ጻድቅ ሰው ለእግዚአብሔር ካለው ፍቅር ይበልጣል"
አባ አርሳኒ

"ሕፃን ልጅ እናቱ ስታጥበው ያለቅሳል:: ሕፃን እምነት (ትንሽ እምነት) ያላቸው ሰዎችም ነፍሳቸውን የሚያጥብ መከራ ሲመጣባቸው እግዚአብሔርን ያማርራሉ" አባ ስምዖን

"ዕለትን የሠጠህ እርሱ ለእለት የሚበቃህንም ይሠጥሃል" ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ

"እጅግ ምርጡ ጸሎት "ጌታ ሆይ አንተ ሁሉን ታውቃለህ የፈቀድከውን አድርግልኝ" ማለት ነው"
ባሕታዊ ቴዎፋን

"ሲያመነዝር ያየኸውን ሰው አንተ ንጹሕ ብትሆንም አትናቀው:: ምክንያቱም አታመንዝር ያለው ጌታ አትፍረድም ብሏል" አባ ቴዎዶር

"አንድ ሰው ኃጢአት ሲሠራ ብታይ እንኳን አትፍረድበት:: አንዳንዴ ዓይንህም ሊሳሳት ይችላል"
ቅዱስ ዮሐንስ ዘሰዋስው

"ለኃጢአተኛው ክንፍህን ዘርጋለት:: ኃጢአቱን ልትሸከምለት ባትችል እንኳን ሸፍንለት"
ቅዱስ ይስሐቅ ሶርያዊ

ከአበው አንዱን ትሕትና ምንድርን ነው? ብለው ጠየቁት:: እርሱም "ትሕትና ማለት ወንድምህ በበደለህ ጊዜ እርሱ ይቅርታ ሳይጠይቅህ በፊት ቀድመህ ይቅር ማለት ነው" አለ::

"ይቅር ካላልክ ገነትም ይቅርብህ" አባ ኤፍሬም አረጋዊ [ If you don’t forgive, forget heaven]

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መስከረም 22 2013 ዓ ም
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን ስለ እኔ ዘንድ ጸልዩ! ሌሎች እንዲያነቡትም የሚከተሉት አድራሻዎች Like እና Share ያድርጉ
FB: https://www.facebook.com/officialHenokhaile/
Telegram: https://www.tg-me.com/የዲ ን ሄኖክ ኃይሌ ትምህርቶች/com.deaconhenokhaile
Instagram: https://www.instagram.com/p/CBnMF0nnhcQ/?igshid=549jvl607bv4
Youtube: https://www.youtube.com/channel/UCOaVsWC05aUjeqIEW3fWj7g
"ውበት ሐሰት ነው ደም ግባትም ከንቱ ነው:: እግዚአብሔርን የምትፈራ ሴት ግን እርስዋ ትመሰገናለች" ምሳ. 31:30

ቅድስት አርሴማን የምናመሰግናት ለዚህ ነው:: ቅድስት አርሴማ (St. Hripsime) በውበትዋ ምክንያት እስከ ሰማዕትነት ድረስ የደረሰች ቅድስት ናት:: በውበትዋ ከተማረከው ከንጉሥ ዲዮቅልጢያኖስ ሸሽታ ወደ አራራት ተራራ ስትሸሽ የአርማንያው ንጉሥ ድርጣድስ (Drtad) ያሳደዳትና እስከ ሰማዕትነት የበቃችው በሚያልፈው ውበት የማያልፈውን አምላክ ላለማጣት ነበር::

ቅዱስ ጳውሎስ ለዕብራውያን

"ከኃጢአት ጋር እየተጋደላችሁ ገና ደምን እስከ ማፍሰስ ድረስ አልተቃወማችሁም" ያለው ቃል ቅድስት አርሴማን አይመለከትም:: ዕብ. 12:4 እርስዋ ከኃጢአት ጋር ደም እስከማፍሰስ ተጋድላለች::
ውበት ሐሰት ነው ደም ግባትም ከንቱ ነው እግዚአብሔር የምትፈራ አርሴማ ግን ትመሰገናለች::
+ በራስህ ክፉ ነገር አታድርግ +

ይድረስ ለተከፋኸው ወንድሜ
መኖር ለደከመህ ፣ ሕይወት ለታከተህ ፣ የሚሰማህ ላጣኸው ፣ የሚረዳህ ሰው ላላገኘኸው መከረኛው ወዳጄ!

ከሞት ውጪ ሌላ መፍትሔ አልታይ ካለህ የአንተ ቢጤ መከረኞቹ ጳውሎስና ሲላስ እስር ቤት ውስጥ ሆነው እንዲህ ይሉሃል::

"በራስህ ክፉ ነገር አታድርግ" ሐዋ. 16:28

አውቃለሁ ዙሪያው ገደል ሆኖብሃል:: ምነው ባልተፈጠርሁ እስክትል ድረስ ተጨንቀሃል::
ግን ይህ ስሜት በአንተ አልተጀመረም:: ሰው ሆኖ ተፈጥሮ ኑሮ ያልመረረው ማን አለ? መሞት ያልተመኘስ ማን አለ?

ሞት ያማረህ አንተን ብቻ መሰለህ?

" ስለ ምን ከማኅፀን አወጣኸኝ? ዓይን ሳያየኝ ምነው በሞትሁ" ያለውን ጻድቅ ኢዮብ አልሰማህም? (ኢዮ. 10:18)

"ከአባቶቼ አልበልጥምና ነፍሴን ውሰድ" ብሎ እንዲሞት የለመነውን ኤልያስን አላየኸውም? 1ነገሥ. 19:4

ዮናስንስ "አሁንም፥ አቤቱ፥ ከሕይወት ሞት ይሻለኛልና እባክህ፥ ነፍሴን ከእኔ ውሰድ፡ አለው" ሲል አልሰማኸውም? (ዮናስ 4:3)

ወንድሜ እመነኝ ምክንያቱ ምንም ይሁን ምን መኖር ያላስጠላው ሰው በታሪክ ፈልገህ አታገኝም::

ሞት ሞት የሸተተው ልቡ የተሰበረ ብዙ ነው:: አንተ ላይ ብቻ የደረሰ ልዩ ፈተና የለም:: "ለሰው ሁሉ ከሚሆነው በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም፤ ነገር ግን ከሚቻላችሁ መጠን ይልቅ ትፈተኑ ዘንድ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የታመነ ነው፥ ትታገሡም ዘንድ እንድትችሉ ከፈተናው ጋር መውጫውን ደግሞ ያደርግላችኋል" ይላል መጽሐፍ:: 1ኛ ቆሮ. 10:13

ምናልባት የልብህን መሰበር የኀዘንህን ጥልቀት አይቶ ምቹ ጊዜ አገኘሁ ብሎ ራስህን እንድትጎዳ ሰይጣን ሊገፋፋህ ይችላል:: እንዴት እንዲህ ዓይነት ሃሳብ በልቤ ሊመጣ ቻለ ብለህ አትረበሽ:: ሰይጣን ይህንን ክፉ ሃሳብ ላንተ ብቻ ሳይሆን ለክርስቶስም አቅርቦለታል::

"የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንህ፥ ወደ ታች ራስህን ወርውር" ብሎ ክርስቶስን እንኳን [ማንነቱን ሳያውቅ] ራሱን እንዲወረውር ሊገፋፋው የሞከረ ደፋር ነው:: የእግዚአብሔር ልጅ የሆነ ሰው ግን ራሱን አይጎዳም:: "ጌታ አምላክህን አትፈታተነው" "ሒድ አንተ ሰይጣን" ብለህ ሰይጣንን ገሠፀው::

ሰይጣን ክርስቶስን "ከሕንፃ ጫፍ በመወርወር የእግዚአብሔር ልጅ መሆንህን አሳይ" ሲለው ክርስቶስ ሰይጣንን ሒድልኝ ብሎ በመገሠጹ በክብር ወደ ሰማይ ዐርጎ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ::
ወንድሜ ሆይ አንተም ሰይጣንን አትስማው ሃሳቡ ራስህን ጎድተህ ከፈጣሪህ እንድትጣላ ሊያደርግህ ነው:: ሰይጣንን ከገሠጽከው በእግዚአብሔር ቀኝ ከበጎቹ ጋር ትቆማለህ::

አሁን ያለህበት ችግር ያልፋል:: የሚሰማህ ክፉ ስሜት መቼም የማይለወጥ አይምሰልህ:: ኀዘኑም ፣ ብቸኝነቱም ፣ ተስፋ ቢስነቱም ያልፋል:: ጨለማው ይነጋል:: የተዘጋው በር ይከፈታል:: ችግሩ ሲፈታ አንተ ከሌለህ ግን ትርጉም የለውም::

ስለዚህ ለሚፈታ ችግር የማይቀለበስ ውሳኔ አትወስን:: ራስን ማጥፋት ከጊዜያዊ ችግር ለመሸሽ ሲሉ ዘላቂ ችግር ውስጥ መግባት ነው:: ጊዜያዊ ሕመምን ለማስታገስ የዘላለም ሕመምን ለምን ትመርጣለህ? "የሞተ ተገላገለ" ሲሉ ሰምተህ እንዳትታለል ሞት ዕረፍት የሚሆነው ራሱ እግዚአብሔር ሲጠራህ ብቻ ነው::
"እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ወደ እኔ ኑ እኔም አሳርፋችኋለሁ" ያለው ጌታ ሳይጠራህ ራስን ማጥፋት የዘላለም ስቃይ ያመጣል::

ወዳጄ "በራስህ አንዳች ክፉ አታድርግ"

የሕይወትህን ዋጋ ታውቅ ይሆን? አንተ እኮ የእግዚአብሔር ልጅ ለአንተ ሲል የሞተልህ ነህ:: ሊፈውስህ የቆሰለ ፣ ሊያከብርህ የተዋረደ ፣ ሊያረካህ የተጠማ ፣ ሊያለብስህ የተራቆተ ለአንተ እኮ ነው::
ክርስቶስ ስለ አንተ ሞቶአል:: አንተን ግን የጠየቀህ እንድትሞትለት ሳይሆን እንድትኖርለት ነው::
ለሞተልህ አምላክ እንዴት መኖር ያቅትሃል?

ወዳጄ ሆይ ሰውነትህ በአምላክ ደም የተገዛ ክቡር ሰውነት ነው:: አካልህ "አንተ" እንጂ "ያንተ" አይደለም:: "በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም፤ ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ" ይላል

ስለዚህ በከበረ የእግዚአብሔር ልጅ ደም የተገዛ ሰውነትህን ለሰይጣን በርካሽ አትሽጠው:: አትግደል የሚለው ሕግ ራስህንም ይጨምራል:: ቤተ መቅደስ የሆነ ሰውነትህን ለማፍረስ አታስብ::
"ማንም የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ቢያፈርስ እግዚአብሔር እርሱን ያፈርሰዋል፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ቅዱስ ነውና፥ ያውም እናንተ ናችሁ" 1ኛ ቆሮ. 3:17

ሰዎች አስቀይመውህ ይሆን?

"አሳያቸዋለሁ ፤ ስሞት የእኔን ነገር ይገባቸዋል" ብለህ በሰዎች ተቀይመህ ራስህን አትጉዳ:: እመነኝ ብትሞት ሰዎች ከሳምንት በላይ አያስታውሱህም:: ለሕይወትህ ዋጋ ያልሠጡ ሰዎች ለሞትህ ዋጋ አይሠጡም:: ፈጥነውም ይረሱሃል:: ለሚረሱህ ሰዎች ብለህ የማይረሳህን አምላክ አታሳዝን:: ሰው ስለ አንተ ግድ የለውም እግዚአብሔር ግን የራስህን ቁጥር ሳይቀር በቁጥር ያውቀዋል :: እንኳንስ ራስህን ልትጎዳ አንዲት ጸጉር እንኳን ከአንተ እንድትወድቅ አይፈልግም::

እግዚአብሔርን በኃጢአት ብታሳዝነው እንኳን ኖረህ ንስሓ እንድትገባ እንጂ እንድትሞት አይፈልግም:: አባትህ ነውና ከእርሱ ጋር ባትሆንም እንድትኖር ይፈልጋል:: በምሳሌ ልንገርህ :-

ሁለት ሴቶች አንድን ሕፃን "የኔ ልጄ ነው" ብለው እየተከራከሩ ጠቢቡ ሰሎሞን ፊት ቀረቡ:: ጠቢቡ ሰሎሞን ሰይፍ አመጣና "ልጁን ቆርጬ ለሁለት ላካፍላችሁ" አላቸው:: አንደኛዋ ሴት "እሺ እንካፈል" ስትል እውነተኛዋ እናት ግን "ልጄ ከሚሞት እርስዋ ትውሰደው" አለች:: እናት መሆንዋም በዚህ ታወቀ::

ወዳጄ ያንተም ኑሮህ ከእግዚአብሔር ጋር ላይሆን ይችላል:: ዓለም የራስዋ አድርጋህም ይሆናል:: በሱስ ውስጥ ትዘፍቀህ ፣ እንደ ሶምሶን በደሊላ እቅፍ ፣ እንደ ዴማስ በተሰሎንቄ ውበት ተማርከህ ይሆናል:: እግዚአብሔር ግን አባትህ ነውና ሞትህን አይፈልግም::

"ልጄ ከሚሞት እርስዋ ትውሰደው" እንዳለችው እናት ፈጣሪህ ከነኃጢአትህም ቢሆን እንድትሞት አይፈልግም:: ከእርሱ ጋር ባትኖርም መኖርህን ይፈልጋል:: "የሟቹን ሞት አልፈቅድምና፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ስለዚህ ተመለሱና በሕይወት ኑሩ" ሕዝ. 18:32

የይሁዳ ኃጢአቱ ጌታውን መሸጡ አልነበረም:: ራሱን መግደሉ ነው:: እግዚአብሔር የሚያዝነው ከበደልህ በላይ በእርሱ ተስፋ ቆርጠህ ራስህን ስትጎዳ ነው::

ወዳጄ የአንተን መኖር የሚፈልጉ ብዙ ናቸው:: ፈጣሪ ወደዚህች ዓለም ያለ ምክንያት አላመጣህም:: በአንተ አለመኖርም የሚጎድል ነገር አለ:: አንተን የሚመስል ሌላ ሰው አልፈጠረምና ለዚህ ዓለም አንተን የሚተካ የለም:: በክብር ወደዚህ ዓለም ያመጣህ አምላክ በክብር ወደራሱ እስኪወስድህ ድረስ "በራስህ ላይ ክፉ ነገር አታድርግ"

"የወኅኒውም ጠባቂ ከእንቅልፉ ነቅቶ የወኅኒው ደጆች ተከፍተው ባየ ጊዜ፥ እስረኞቹ ያመለጡ መስሎት ራሱን ይገድል ዘንድ አስቦ ሰይፉን መዘዘ።
ጳውሎስ ግን በታላቅ ድምፅ፦ ሁላችን ከዚህ አለንና በራስህ ክፉ ነገር አታድርግ፡ ብሎ ጮኸ" ሐዋ. 16:27-28

ይህ ሰው እስረኛ ያመለጠ መስሎት ራሱን ሊያጠፋ ሲል ጳውሎስ "ሁላችን ከዚህ አለንና በራስህ ክፉ ነገር አታድርግ" አለው::

ወዳጄ አንተስ ተስፋ የቆረጥኸው ምን ያመለጠ መስሎህ ነው?
የትምህርት ዕድል ያመለጠህ መስሎህ ነው? ገና ሺህ የትምህርት ዕድሎች አሉህ:: ዕድሜህ ያመለጠህ መስሎህ ነው? ነገ የሚጠብቁህ ብሩሕ ዘመናት እኮ ቁጭ ብለው አሉ? የሚረዳኝ ሰው የሚያስብልኝ ሰው አጥቼያለሁ? ብለህ ከሆነም ካልሰሙህ ጥቂቶች በላይ ልንሰማህ የምንሻ "ሁላችን ከዚህ አለንና በራስህ ክፉ ነገር አታድርግ"

መከራ ጸናብኝ ኑሮ ጨለመብኝ የሀገሪቱ ሁኔታ ተስፋ አሳጣኝ ብለህ ይሆን? እኛስ አብረንህ አይደልንም? አብረን ከገባንበት ችግር አብረን ብንወጣ አይሻልም? ከአንተ በባሰ ሁኔታ የታሰርንና የተገረፍን ጳውሎሶችና ሲላሶች "ሁላችን በዚህ አለንና በራስህ ክፉ አታድርግ" ስንልህ ስማን::

ይልቅ አንተም እንደ ወኅኒው ጠባቂ "እድን ዘንድ ምን ላድርግ ብለህ?"ነፍስህን የምታድንበትን መንገድ ወደ መቅደሱ ቀርበህ ጠይቅ::

ወዳጄ ይህንን ጽሑፍ ያነበብኸውም በሕይወት ስላለህ ነው:: የአንተን ዓይን የሚጠብቁ ብዙ ጽሑፎች ፣ የአንተን ጆሮ የሚፈልጉ ብዙ ድምፆች ፣ የአንተን መሐረብ የሚፈልጉ ብዙ ዕንባዎች ፣ የአንተን ሳቅ የሚፈልጉ ብዙ ቀልዶች ... ገና ብዙ ብዙ አሉ::

ስለዚህ ሰይጣንን አሳፍረው:: እንዲህ በለው :-

"ጠላቴ ሆይ፥ ብወድቅ እነሣለሁና፥ በጨለማም ብቀመጥ እግዚአብሔር ብርሃን ይሆንልኛልና በእኔ ላይ ደስ አይበልሽ" ሚክ. 7:8

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ጥቅምት 2016 ዓ.ም.
ሜልበርን አውስትራሊያ

ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን አጥብቃችሁ ስለ እኔ ጸልዩልኝ!
በኮሜንት መስጫው ሥር "ለሚሰሙት ጸጋን ይሰጥ ዘንድ፥ እንደሚያስፈልግ ለማነጽ የሚጠቅም ማናቸውም በጎ ቃል እንጂ [ዋጋን በምድር የሚያስቀር ውዳሴም ሆነ ሌላ] ክፉ ቃል ከአፋችሁ ከቶ አይውጣ" (ኤፌ 4:29)
ነቢያት ጌታ "ይወርዳል ይወለዳል" ብለው የተናገሩት ትንቢት እንዲፈጸም ተመኝተው ጾሙ ጸለዩ:: እኛ ስለምን እንጾማለን? ክርስቶስ ተወልዶ ፣ ተጠምቆ ፣ አስተምሮ ፣ ተሰቅሎ ፣ ሞቶ ፣ ተነሥቶ ፣ ዐርጎ ፣ በአባቱ ቀኝ አይደለምን? አሁን ለምን እንጾማለን? ብለን እናስባለን::

ጌታ በእኔና አንተ ልብ ውስጥ እውነት ተወልዶአልን? እውነት የእኛ ልብ እንደ ቤተልሔም ግርግም ለክርስቶስ ማደሪያ ሆኖአል? ማደሪያ አሳጥተን ከእናቱ ጋር አልመለስነውም?

የጥምቀቱ ትሕትና በእኛ ልብ መቼ ደረሰ? የስቅለቱ ሕማም መች በእኛ ሕሊና ተጻፈ? የትንሣኤው ተስፋ የዕርገቱ ልዕልና በእኛ ልቡና መቼ ዐረፈ?

ስለዚህ ነቢያት "ውረድ ተወለድ" ብለው የጾሙትን ጾም እንጾማለን:: ጌታ ሆይ በእኔ ሕይወትም ውስጥ ውረድ ተወለድ የእኔን ሰውነት ማደሪያህ አድርገው:: ሕዋሳቶቼ ከኃጢአት አርፈው እንደ ቤተልሔም ግርግም ማደሪያህ ይሁኑ::

የቤተልሔም እንስሳት ትንፋሽ ገበሩልህ ፣ የቢታንያ ድንጋዮች ዘማሪ ቢጠፋ ሊዘምሩ ዝግጁ ነበሩ ፣ የቤተ መቅደስ መጋረጃ ለክብርህ ተቀደደ ፣ ጨረቃ ላንተ ደም ለበሰች ፣ ፀሐይ ስላንተ ጨለመች ፣ ከዋክብት ለስምህ ረገፉ ፣ ዓለቶች ለፍቅርህ ተሰነጠቁ::

ከቤተልሔም እንስሳት ፣ ከቢታንያ ድንጋዮች ፣ ከቤተ መቅደስ መጋረጃ እኔ እንዴት አንሼ ልገኝ? የቢታንያ ድንጋይ ያወቀህን ያህል ሳላውቅህ ፣ የቤተ መቅደስ መጋረጃ የተረዳህን ያህል ሳልረዳህ እንዴት ልኑር?

ዓለት ላንተ ሲሰነጠቅ የኔ ልብ ለምን ከዓለት ደነደነ? ጨረቃ ደም ስታለቅስ እኔ መከራህ ለምን አልተሰማኝም?
ሙታን በሞትህ ሲነሡ እኔ ምነው ከኃጢአት ሞት መነሣት ተሳነኝ?

ለዚህ ነው በእኔ ሕይወት ገና አልተወለድክም የምለው::

ስለዚህ ጌታ ሆይ የነቢያትህን ጾም ጸሎት ሰምተህ የወረድህ የተወለድህ ጌታ ሆይ በእኔም ሕይወት ውረድ ተወለድና እኔም ከመላእክት ጋር አብሬ ልዘምር ፣ ከሰብአ ሰገል ጋር ሥጦታህን ልቁጠር ፣ ከእረኞች ጋራ ልደነቅ:: ልደትህ ሳይገባኝ ምጽዓትህ እንዳይደርስብኝ እርዳኝ::

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ጾመ ነቢያት 2015 ዓ.ም. የተጻፈ
የበሬን ምስጋና ወሰደው ፈረሱ (ርእስ)

የአእላፋት ዝማሬን ዕውን ለማድረግ ላለፉት ሦስት ወራት እንቅልፍ ያጡ ፣ የታመሙ ፣ ልባቸው በስድብና በሽሙጥ ንግግር የቆሰለ ፣ በረዣዥም ስብሰባዎችና የጉልበት ሥራዎች የዛሉ ፣ ዝግጅቱን በዚህ ደረጃ ከፍ እንዲል ሰዎችን አሳምኖ ገንዘብ በማሰባሰብ የተንከራተቱ ፣ በአንድ ትንፋሽ ሠላሳ መዝሙር ሲያጠኑ የከረሙ ፣ መዝሙር ለማስቀረጽ ሥራ ትተው በስቱድዮ የዋሉ ፣ ሦስት ጊዜ revise የተደረገውን Stage design የሠሩ ፣ በመሐረነ አብ ጸሎት በየአድባራቱ ደጅ የጠኑ ፣ የዘማርያን ልብስና ልብሰ ተክህኖ ዲዛይን ሲያደርጉ ፣ ተነግሮ የማያልቅ ድካም የደከሙ ትሑታንና ታዛዦች የሆኑ የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ትውልድ የቦርድና የሥራ አስፈጻሚ አባላት ፣ የጃን ያሬድ ኅብረ ዝማሬ መዘምራን ፣ የጃን አጋፋሪ event organizing ቡድንና በሥሩ የተቋቋሙ 15 ቡድኖች ፣ የጃን አግናጥዮስ የሕፃናትና አዳጊዎች project አባላት ፣ የጃን እስጢፋኖስ ዲያቆናት ፣ የጃንደረባው ሚድያ እሳት የላሱ የካሜራና ኤዲቲንግ የግራፊክስ ባለሙያዎችና የማኅበራዊ ሚድያ ዘመቻ ወጣቶች የአእላፋት ዝማሬን እውን ለማድረግ የከፈሉት መሥዋዕትነት እጅግ ብዙ ነው::

ለዚህ አገልግሎት ምስጋና የሚገባው ዕንባና ተማጽኖአችንን ያልናቀ ልዑል እግዚአብሔር ነው::

ዓለም ዘመኑ ጥሩ አይደለም ብላ ስካሩን ጭፈራውን ፈንጠዝያውን ግድያውን አላቆመችም:: እኛም ስብሐተ እግዚአብሔር የወቅቱን ሁኔታ እያየች የማታስታጉል ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች እንደመሆናችን ሲከፋን የምንተወው ደስ ሲለን የምንቀጥለው መዝሙር የለም ብለው ለጸሎተ ምሕላና ለአእላፋት ዝማሬ የተሠጡ ወጣቶች ብዙ ናቸው:: "አርምሞ ጽርዓት በሌለበት ምስጋና ሳናቋርጥ ዘወትር እናመሰግንሃለን:: ይኸውም ሊቃነ መላእክት የሚያመሰግኑህ ምስጋና ነው" (ጸሎተ ኪዳን)

ምግብ ቤት ገብተን ጥሩ ስንበላ አስተናጋጁን እናመሰግናለን:: ቲፕ እንሠጠዋለን:: ማዕድ ቤት ውስጥ እሳት የበላቸውን ሼፎችና ተባባሪ ሠራተኞች ግን አናያቸውም:: የአእላፋት ዝማሬንም በተመለከተ ሊመሰገን የሚገባው እንቅልፉን የሠዋ ብዙ ወጣት ከጀርባ አለና አስተናጋጁን ለቀቅ አድርጋችሁ ሼፎቹ ላይ አተኩሩ::
ከዚያ ውጪ ግን ከታመነበት ተአምር መሥራት የሚችለውን ቅን 1/21ኛውን ጃን ያሬድ ብቻ ሳይሆን መላውን የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ትውልድ በጸሎት በገንዘብ በሃሳብ ደግፉ::

የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ትውልድን ለመደገፍ

https://donate.janderebaw.org/

በቴሌ ብር
Merchant ID 777582
The Ethiopian Jandereba Generation

8261
Commercial Bank of Ethiopia

8261
Abyssina Bank

Janderebaw Media
የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ትውልድ The Ethiopian Jandereba Generation
በከበረች ጸሎቱ ይቅር ይበለንና ራሱን በትሕትና "ከጌቶች ልጆች የሚወድቀውን ፍርፋሪ የሚለምን ውሻ" ብሎ የሚጠራው ሶርያዊው ኮከብ ቅዱስ ኤፍሬም በየድርሰቶቹ መካከል እንዲህ እንዲህ አለ:-

"ጌታችን ከሣምራዊትዋ ሴት ጋር በተነጋገረ ጊዜ በንግግራቸው መጀመሪያ ማንነቱን አልገለጠላትም። መጀመሪያ ያየችው ውኃ የጠማውን ሰው ነበር ፣ ከዚያ አይሁዳዊ ፣ ከዚያ መምህር (ረቢ) ፣ ቀጥሎ ነቢይ ከሁሉም መጨረሻ መሲህ መሆኑን አየች።
ውኃ የተጠማውን ሰው በንግግር ልትረታ ስትሞክር በአይሁዳዊ ላይ ያላትን ጥላቻ አሳየች። ከመምህሩ ጋርም ተከራከረች ፣ ከነቢዩ እግር ስር ተንበረከከች ፣ መሲሁንም ወደደችው"
ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ (ስለ ሣምራዊቷ ሴት ዮሐ 4:1)

★ ★ ★

"ጌታ ሆይ ለእኛ ፊት ክብርን የሠጠ እንደ አንተ ያለ ማን አለ?
የዕውሩን ዓይን ባበራህለት ጊዜ ላድነው ነህ ብለህ በፊቱ ላይ አልተፋህበትም።
ነገር ግን አርኣያችንን አክብረህ በመሬት ላይ እንትፍ ብለው ፈወስከው።
ጌታዬ ሆይ በእኔ ላይ ግን በፊቴ ላይ እንትፍ በልብኝ ፣ በፈቃዴ ያጠፋሁትን ዓይኔን በፈቃድህ አብራልኝ"

ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ
(ዕውር ሆኖ ስለተወለደው ዮሐ 9:30)

★ ★ ★
"ጌታ ሆይ ዕውሩን ሂድ ብለህ ወደላክህበት ወደ ሰሊሆም መጠመቂያ አሁን ልንሔድ አንችልም። ነገር ግን ሕይወትንና ብርሃንን የተሞላው የከበረ ደምህ ያለበት ጽዋ በእኛ ዘንድ አለ። ከእርሱ በተቀበልን ቁጥር እንነጻለን" ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ

★ ★ ★

"ጌታዬ ሆይ በሔድኩበት ውጣውረድ የተሞላ መንገድ እምነቴ ደከመ ፣ መንገዱ የሚወስደኝም በግራ ወደሚቆሙት ፣ በደጅ ቆመው ክፈትልን ሲሉህ "አላውቃችሁም" ከምትላቸው ወገን ልሆን ነው።
ጌታዬ ሆይ እኔ አውቅሃለሁ ፣ አንተ ግን አላውቅህም ትለኝ ይሆን? አቤቱ በአንተ ለማምን ለእኔ ለኃጢአተኛው ራራልኝ። ብበድልህም እንኳን አሁንም በርህን እያንኳኳሁ ነው። እየተጎተትኩም ቢሆን አሁንም የምጓዘው ወደ አንተ ለመምጣት ነው"

ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ (ማቴ 7:7)
★ ★ ★

"ጌታ ሆይ እነዚህን በዕድሜ ሕፃናት የሆኑ የመንፈስ ልጆቼን ይቅር በላቸው። ሕፃን የነበርከው ሆይ የሕፃንነትህን ጊዜ አስብ። ልጅነታቸው ያንተን ልጅነት እንዲመስል አድርግላቸውና በቸርነትህ አድናቸው"
ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ከተለያዩ መዝሙራቱ (Hymns) በተርጓሚው ተለቃቅሞ የተሰበሰበ
ኅዳር 26 2011 ዓ ም
ክርስቲያን ሳንድ
Deacon Henok Haile
+ ከሁሉ በኋላ ጭንጋፍ ለምሆን ለእኔ ታየኝ +

ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ምእመናን ስለ ጌታ ትንሣኤ ማስረጃ እያቀረበ ነው:: በዚያን ዘመን ለጌታ ትንሣኤ ማስረጃ ስትጠቅስ በማቴዎስ ወንጌል እንዲህ ይላል ብለህ እንዳትጠቅስ ገና ወንጌላት አልተጻፉም:: ቢጻፉም ማቴዎስ በሕይወት እያለ በቃሉ መመስከር ሲችል ጽሑፉን ማስረጃ ማድረግ አያስፈልግህም:: ስለዚህ ለመነሣቱ ማስረጃዎች ከተነሣ በኋላ ያዩት ሰዎች ነበሩ:: በሕይወት ያሉትን የዓይን ምስክሮችን መጥቀስ ይቻላል:: የዓይን እማኞች ምስክርነት ከጽሑፍ በላይ የታሪክ ማስረጃ ነው:: ስለዚህ ጳውሎስ ስለ ጌታ ትንሣኤ "እነ እገሌ አይተውታል" እያለ መዘርዘርን መረጠ::

ጌታ ከተነሣ በኋላ እንደ ቀድሞው ለሁሉ አልታየም:: እርሱን ለማየት የተገባቸው ጥቂት ወደ ሺህ የሚጠጉ ሰዎች ነበሩ:: በማኅበር ያዩት አሉ:: በግል ያዩት አሉ::
ያዩት ነገር ወንጌል የሆነላቸው ብፁዓን ዓይኖች ያሏቸው እንዴት የታደሉ ናቸው? የተሰቀለውን ተነሥቶ ያዩት! ዳግም በሚመጣበት አካል የተገለጠላቸው ምንኛ የታደሉ ናቸው? ከመድኃኔ ዓለም አፍ ተቀብለው ኪዳን ያደረሱ! የጌታን ቅዳሴ ተቀብለው ያስቀደሱ! የትንሣኤው ማግስት ምስክሮች እንዴት ዕድለኞች ናቸው? ቢሞቱም እንኳን መነሣታቸውን በጌታ ትንሣኤ አይተው ደስ ብሎአቸው ያንቀላፉ እነርሱ ምንኛ የታደሉ ናቸው?

ቅዱስ ጳውሎስ በወንጌል ከተጠቀሱት ከነ ኬፋ በተጨማሪ ለይቶ ጌታ ለማን ለማን እንደታየ ገለጸ:: ለያዕቆብ ታየ ብሎ የእልፍዮስን ልጅ ለይቶ ጠቀሰው:: የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፍት እንደሚሉት ይህ ሐዋርያ ከሌሎች በተለየ የጌታን ትንሣኤ ሳላይ እህል አልቀምስም ብሎ የተሳለና አክፍሎትን የጀመረ ነበርና ጌታ ለይቶ ክብሩን አሳይቶታል:: ከዚያም ለዐሥራ ሁለቱ ታየ ብሎ የጌታን ድኅረ ትንሣኤ አስተርእዮ ዘረዘረ:: እኔ ማለትን የማይወደው ትሑት ቅዱስ ጳውሎስ "ከሁሉ በኋላ እንደ ጭንጋፍ ለምሆን ለእኔ ደግሞ ታየኝ አለ::

ጭንጋፍ ምንድር ነው? ጭንጋፍ (ጸዕጻዕ/ ተውራድ) ለፅንስ የሚነገር ቃል ነው:: መወለድ ያለበትን ጊዜ ያልጠበቀ ያለ ጊዜው የተወለደ ፅንስ ነው:: በመጠኑ ከሌላው ጊዜውን ከጠበቀ ፅንስ የሚያንስ ሲሆን ዕድገቱን በተገቢው ጊዜ ከሚወለድ ልጅ ጋር ለማስተካከል ሲባል በሙቀት ማቆያ ክፍል እንዲቆይ ይደረጋል:: ይህ ፅንስ ሲወለድ በሕመም ውስጥ ሆኖ ተሰቃይቶ ተጨንቆ ነው::

ቅዱስ ጳውሎስ ራሱን ለመግለጽ የተጠቀመበት ይህ አንድ ቃል የሕይወት ታሪኩን ጠቅልሎ የያዘ ድንቅ ቃል ነበር::
ቅዱስ ጳውሎስ ምንም እንኳን የቤተ ክርስቲያን ብርሃን የሆነ ሐዋርያ ቢሆንም እንደ ዓሥራ ሁለቱ ሐዋርያት በጊዜው የተጠራ አልነበረም:: እርሱ ከሐዋርያት ጋር አብሮ በዳግም ልደት የተወለደ ሳይሆን ያለ ጊዜው ክርስቶስ ባረገ በስምንተኛው ዓመት የተጠራ ነበረና ራሱን ካለ ጊዜው ከተወለደው ፅንስ ጋር አመሳስሎ እንደ ጭንጋፍ የምሆን ብሎ ጠራ::

ጭንጋፍ ሲወለድ በመጠኑ ከሌላው ፅንስ ያነሰ ይሆናል::
ቅዱስ ጳውሎስም ራሱን ጭንጋፍ ካለ በኋላ "እኔ ከሐዋርያት ሁሉ የማንስ ነኝና፥ የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ስላሳደድሁ ሐዋርያ ተብዬ ልጠራ የማይገባኝ" ብሎ አብራርቶታል:: (1ቆሮ 15:9)

ልጅ ጭንጋፍ ሆኖ ሲወለድ በሥቃይ ነው:: ጤና ያጣል ይታመማል:: እናቲቱም ትታወካለች በድብታ በጭንቀት ትቸገራለች:: ባለሙያዎቹ እንደሚሉት እናት ያለ ጊዜው ከተወለደ ልጅዋ ጋር እናታዊ ትስስር ለመፍጠርና የእናትነት ፍቅርዋን ለመሥጠት ባልጠበቀችው ጊዜ የመጣ በመሆኑ ምክንያት ለጥቂት ጊዜ ትቸገራለች:: በአጭሩ ጭንጋፍ ሆኖ ሲወለድ እሱም ይሰቃያል እናቱንም ያስጨንቃል:: ወዲያው እንደሌላ ሕፃን በሰው እጅ አይታቀፍም:: ከተፈጥሮአዊ እስከ ሰው ሠራሽ እንደየጊዜው እየዘመነ በሔደው የልጅ ሙቀት መስጫ መንገድ እየታገዘ የሰውነት አካሎቹ በአግባቡ መሥራት እስከሚችሉና በሽታ መቋቋም እስከሚችል ይቆያል::

ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ጭንጋፍ ነበርኩ ያለው ለዚህ ነው:: በዳግም ልደት የተወለደው በደማስቆ መንገድ ወድቆ ሊቋቋመው ባልቻለው ብርሃን ተመትቶ ነበር:: "ሳውል ሳውል ስለምን ታሳድደኛለህ?" የሚል ድምፅ ሲሰማ ፅንስ ነውና ዓይኑን እንኳን መግለጥ አልቻለም ነበር::
ከተወለደ በኋላም ወዲያው ወደ ቤተ ክርስቲያን እቅፍ ወደ ሐዋርያት ማኅበር አልገባም:: እንደ ጭንጋፍ የምሆን እንዳለ ሙቀት ያስፈልገው ነበርና የሰው እጅ ሳያቅፈው ሦስት ዓመት በሱባኤ ቆይቶ በመንፈስ ቅዱስ ተማወቀ::

"ነገር ግን በእናቴ ማኅፀን ሳለሁ የለየኝ በጸጋውም የጠራኝ እግዚአብሔር በአሕዛብ መካከል ስለ እርሱ ወንጌልን እሰብክ ዘንድ ልጁን በእኔ ሁኔታ ሊገልጥ በወደደ ጊዜ፥ ወዲያው ከሥጋና ከደም ጋር አልተማከርሁም፥ ከእኔም በፊት ሐዋርያት ወደ ነበሩት ወደ ኢየሩሳሌም አልወጣሁም፥ ነገር ግን ወደ ዓረብ አገር ሄድሁ እንደ ገናም ወደ ደማስቆ ተመለስሁ። ከሦስት ዓመት በኁዋላ ወደ ኢየሩሳሌም ወጣሁ" ብሎ ስለ መንፈሳዊ ኃይል መልበሱ ይናገራል:: (ገላ 1:15-18)

ጭንጋፍ ሆኖ የተወለደ ልጅ የሚገጥመው ችግር ከወላጆቹ ጋር በሥነ ልቡና ለመተሳሰር መቸገሩ ነው::
ቅዱስ ጳውሎስን ለማመንና እንደ ልጅ ለመቀበል የቤተ ክርስቲያን ማኅበርም ተቸግራ ነበር::
"ሳውልም ወደ ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ ከደቀ መዛሙርት ጋር ይተባበር ዘንድ ሞከረ፤ ሁሉም ደቀ መዝሙር እንደ ሆነ ስላላመኑ ፈሩት" ሐዋ 9:26 ስለዚህ ሐዋርያው እንደ ጭንጋፍ ነኝ አለ::

ቅዱስ ጳውሎስ ስለ ጌታ መነሣት ምስክሮች ብሎ ሌሎችን ከዘረዘረ በኋላ "ከሁሉ በኋላ ጭንጋፍ ለምሆን ለእኔ ታየኝ" ብሎ ተናገረ:: ክርስቶስ ተነሥቶአል ወይ ብለው ሲጠይቁህ አዎ ተነሥቶአል እነ እገሌ አይተውታል ብለህ ዘርዝረህ
"ከሁሉ በኁዋላ ለእኔም ታየኝ" ብለህ መናገር መቻል እንዴት መታደል ነው!?

ወዳጄ ክርስቶስ መነሣቱን ታምናለህ:: ልክ ነህ ለብዙዎች ታይቶአል:: አንተስ ከሁሉ በኁዋላ ለእኔም ታየኝ ማለት ትችል ይሆን? ጌታ ከተነሣ በኁዋላ ላለፉት ሁለት ሺህ ዓመታት ለብዙዎች ታይቶአል:: ብዙዎቹ ቅዱሳን አይተውታል:: ቅዱስ እስጢፋኖስ አይቶታል : ቅድስት አርሴማ አይታዋለች : አቡነ ተክለ ሃይማኖት አይተውታል : አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ተመልክተውታል:: አባ ጳኩሚስ በዕንባ ተመልክቶታል : ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ አይታዋለች::

ሁሉም ቅዱሳን ብዕር ቢሠጣቸው ከዕንባ ጋር
"ከሁሉ በኁዋላ ለእኔም ታየኝ" ብለው የትንሣኤውን ማስረጃ ዝርዝር ይቀጥላሉ:: ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ በበረሃ ሲጸልይ አይቶት ነበርና ሰው ባገኘ ቁጥር
ወቅቱ የፋሲካ ሰሞን ባይሆንም እንኳን በፈገግታ ተሞልቶ
"ክርስቶስ ተነሥቶአል!" ብሎ ያበሥርና ሰላምታ ይሠጥ ነበር::

ጌታ ሆይ ለእኔ ለኃጢአተኛው የምትታየኝ መቼ ይሆን? ቸርነትህን አይቻለሁ! ፍቅርህን አይቻለሁ! ብሩሕ ገጽህን የማየው መቼ ይሆን? መች እደርሳለሁ የአምላኬንስ ፊት መቼ አየዋለሁ? እኔም እንደ ቅዱሳንህ "ከሁሉ በኁዋላ ለእኔ ታየኝ" ብዬ የተቀመጠውን ብዕር አንሥቼ የምጽፈው መቼ ይሆን? አቤቱ ፊትህን እሻለሁ! አቤቱ ፊትህን ከእኔ አትመልስ! አቤቱ ፊትህን እሻለሁ!

"ኢየሱስ ክርስቶስ በግዕ ዘቀራንዮ
ለላሕይከ ንትሜነይ ከመ ንርአዮ"
"የቀራንዮው በግ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ
ውበትህን ልናየው እንመኛለን"

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን ስለ እኔ ዘንድ ጸልዩ! ሌሎች እንዲያነቡትም የሚከተሉት አድራሻዎች Like እና Share ያድርጉ
FB: https://www.facebook.com/officialHenokhaile/
Telegram: https://www.tg-me.com/የዲ ን ሄኖክ ኃይሌ ትምህርቶች/com.deaconhenokhaile
Instagram: https://www.instagram.com/p/CBnMF0nnhcQ/?igshid=549jvl607bv4
Youtube: https://www.youtube.com/channel/UCOaVsWC05aUjeqIEW3fWj7g
+ ትሞታለህና ቤትህን አስተካክል +

ንጉሥ ሕዝቅያስ በጠና ታምሞ ተኝቶአል:: ነቢዩ ኢሳይያስ ሊጠይቀው መጣ:: ሆኖም እንደ ልማዱ እግዚአብሔር ይማርህ አላለውም:: ለጆሮ የሚከብድ ቃል ጥሎበት ወጣ:: "ትሞታለህና ቤትህን አስተካክል!"

ነቢዩ ይህንን ብሎት ከወጣ በኁላ ሕዝቅያስ ወደ ግድግዳው ዞሮ ስቅስቅ ብሎ አለቀሰ:: አምላኩ በንግግር ብዛት የሚሰማ አምላክ አይደለምና ፊቱን ወደ መቅደሱ አቅጣጫ አዙሮ አለቀሰ::

ከጥቂት ደቂቃ በኁዋላ ነቢዩ ኢሳይያስ ሌላ መልእክት ይዞ ተመለሰ:: እግዚአብሔር እንዲህ ይላል :- ጸሎትህን ሰምቻለሁ ዕንባህን አይቻለሁ በዕድሜህ ላይ ዐሥራ አምስት ዓመት እጨምራለሁ" (ኢሳ 38:5)

ሕዝቅያስ ቤትህን አስተካክል ከተባለ በኁዋላ ፊቱን አዙሮ ከማልቀስ በቀር ምንም አላደረገም:: ሕዝቅያስ ሆይ ከአልጋህ ሳትወርድ ያስተካከልከው ቤት ምን ዓይነት ቤት ነው? ለባሪያዎችህ መመሪያ ሳትሠጥ የምታስተካክለው ቤትስ እንዴት ያለ ነው? በደቂቃዎች ውስጥ ትሞታለህ ከተባልክ በኁዋላ ዐሥራ አምስት ዓመት ያስጨመረልህ ምን ዓይነት ማስተካከያ አድርገህ ነው? ለእኛም ንገረንና ዕድሜ እናስጨምር::

ሕዝቅያስ ከአልጋው ሳይነሣ ያስተካከለው ቤቱ ልቡ ነበር::
ልብህን ካስተካከልህ ቤትህ ይስተካከላል:: እግዚአብሔር እንደሆን ትሞታለህ ቢልህም መሞትህን አይፈልግም:: እርሱ ካንተ ጋር ጸብ የለውም::

"በውኑ ኃጢአተኛ ይሞት ዘንድ እፈቅዳለሁን? ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ከመንገዱስ ይመለስና በሕይወት ይኖር ዘንድ አይደለምን?" ይላል መሐሪው (ሕዝ 18:23)

እርሱ ትሞታለህ የሚልህ መኖርህን ፈልጎ ነው:: አንዴ ብያለሁ ብሎ አይጨክንብህም:: በንስሓ ተመለስ እንጂ ምሬሃለሁ ለማለት ይቸኩላል:: አሁን ትሞታለህ ብዬው አሁን ትድናለህ ብለው ይንቀኛል ሳይል ተመልሶ ይምርሃል:: ኃጢአትህንም ወደ ጥልቁ ይጥለዋል:: በጎ እንድትሠራም ዕድሜ ይጨምርልሃል:: አንተ ብቻ ተመለስና አሁኑኑ ንስሓ ግባ::
ከበደል አልጋ ጋር ያጣበቀህን ፈተናም ድል መንሻው ጊዜ አሁን ነው:: ሕዝቅያስ በደቂቃ ዕንባ ምሕረት አግኝቶ ዕድሜ ካስጨመረ በዐቢይ ጾም ሙሉ የሚያለቅስ ምን ያህል ዕድሜ ያገኝ ይሆን?
ወዳጄ አንተም ተነሣና በዚህ ወር ቤትህን አስተካክል::
እንደ ሕዝቅያስ ፈጣሪህ ይጠብቅሃል:: የተቀየምከውን ይቅር በል የበደልከውን ካስ የሚበቀልህን የማይተኛ ጠላትህን ዲያቢሎስ ተበቀለው::

የዐቢይ ጾም የወንጌል ምንባብ ስለ ዲያቢሎስ ፈተና ሦስቱ ወንጌላት የተናገሩትን ስናስተውል ሦስት ዓይነት ጥቅሶች እናገኛለን::

አርባ ቀን ከዲያብሎስ ተፈተነ። (ሉቃ 4:2)

በምድረ በዳም ከሰይጣን እየተፈተነ አርባ ቀን ሰነበተ (ማር 1:13)
የሚሉት ቃላት ጌታችን ዐርባውንም ቀን መፈተኑን ያሳያሉ::

አርባ ቀንና አርባ ሌሊትም ከጦመ በኋላ ተራበ። ፈታኝም ቀርቦ እንዲህ አለው (ማቴ 4:2)

የሚለው ደግሞ ከጾሙ በኁዋላ የቀረቡለትን ሦስት ፈተናዎች የሚያሳይ ነው::
ሦስተኛው ጥቅስ ደግሞ ከተፈተነ በኁዋላ ያለው ሲሆን

ዲያቢሎስም ፈተናውን ሁሉ ከጨረሰ በኋላ እስከ ጊዜው ከእርሱ ተለየ። (ሉቃ 4:13) ይላል:: ዲያቢሎስ ፈተናውን ቢጨርስም የሚተወው ለጊዜው እንጂ መፈተኑን አያቆምም:: የዲያቢሎስ ፈተና ስልቱ ይቀያየራል እንጂ ይቀጥላል::

ዐቢይ ጾም ዲያቢሎስ ድል የተደረገበት የጦር ዐውድማ ነው:: በዚህ ወራት ድል ያላደረግነውን ፈተና በሌላ ጊዜ አናደርገውም:: ሰነፍ ገበሬ በሰኔ ይሞታል እንደሚባለው በዐቢይ ጾም የተኛ ክርስቲያን መቼም አይነቃም:: ከነስሙ ሁዳዴ (ሰፊ እርሻዬ) የምንለው ይህ ጾም ለነፍሳችን ብዙ ዘር የምንዘራበት አጋንንት መድረሻ የሚያጡበት ጾም ነው:: በዐቢይ ጾም ያልተገራ አንደበት መቼም አይገራም:: በዐቢይ ጾም ያልተፈወሰ ቂም መቼም አይፈወስም::

ጌታችን በወንጌል አንዴ ወደ እሳት አንዴ ወደ ውኃ የሚጥል ጋኔን ያለበትን ልጅ ሲፈውስ "ይህ ዓይነቱ ጋኔን ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም" ብሎ ነበር:: ሀገራችንን አንዴ ወደ እሳት አንዴ ወደ ውኃ የሚጥላት የጥላቻ ጋኔንም ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም::

ወዳጄ ከቁስልህ የምትፈወስበት ወር እንደደረሰ ዕወቅ:: አንተስ ብትሆን ልትላቀቀው እየፈለግህ ያቃተህ ክፉ ልማድ የለብህም:: እንደ ቅዱስ ጳውሎስ "የምፈልገውን መልካም ነገር አላደርግም የማልፈልገውን ክፉ ነገር ግን አደርጋለሁ:: ምንኛ ጎስቋላ ለዚህ ለሞት ከተሠጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?" ብለህ ምርር እንድትል ያደረገህ ኃጢአት የለም? እንግዲያውስ እወቀው:: ይህ ዓይነቱ ወገን ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም:: ይህ ጾም ቁስል የሚሽርበት ጾም ነው:: ይህ ጾም ሸክም ማራገፊያ ጾም ነው:: እንደ ሕዝቅያስ በዚህ ወር ቤትህን በንስሓ አስተካክል::

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
የካቲት 15 2012 ዓ ም
ዝዋይ ኢትዮጵያ
"ይህችን ዓመት ተወኝ!"

ከዓመት እስከ ዓመት - ፍሬን ሳላፈራ - ደረቅ እንደሆንኩኝ
በራድ ወይም ትኩስ - ሁለቱንም ሳልሆን - እንዲያው ለብ እንዳልኩኝ
አለሁኝ በቤትህ - ለሙን መሬትህን - እያጎሳቆልኩኝ
አውቃለሁ አምላኬ - ፍሬዬን ለመልቀም - እንዳመላለስኩህ
ዛሬም ሳላፈራ - እሾህን አብቅዬ - ደርቄ ጠበቅሁህ
ያልተደረገልኝ - ያላፈሰሰክብኝ - ያልሰጠኸኝ የለም
ነገር ግን ይህ ሁሉ - አላርምህ አለኝ - አልለየኝም ከዓለም
የማትሰለቸኝ ሆይ - ተነሥቼ እስክቆም - እባክህ ታገሠኝ
የእኔን ክፋት ተወው - መልአክህን ሰምተህ - ይህችን ዓመት ተወኝ!

አውቃለሁ ታውቃለህ - ቀጠሮን ሰጥቼ - እንደማላከብር
ብዙ ጊዜ አቅጄ - ብዙ ጊዜ ዝቼ - በወሬ እንደምቀር
‹ዘንድሮስ…!› እንዳልኩኝ - አምና ይሄን ጊዜ - ሰምተኸኝ ነበረ
ምንም ሳልለወጥ - ‹ዘንድሮዬ› አልፎ - በአዲስ ተቀየረ
ፍሬ የማይወጣኝ - እኔን በመኮትኮት - እጆችህ ደከሙ
እኔ ግን አለሁኝ - ዛሬም አልበቃኝም - በኃጢአት መታመሙ
የቃልህን ውኃ - በድንጋይ ልጅህ ላይ - ሳትታክት ስታፈስስ -
ዘመን ተቆጠረ
ወደ ልቤ ሳይሰርግ - ሕይወቴን ሳይለውጥ - እንዲያው ፈስሶ ቀረ
ቃልህን ጠግቤ - እያገሳሁት ነው - ሌሎች እስኪሰሙ
በቃልህ መኖር ግን - አልያዝህ አለኝ - ከበደኝ ቀለሙ
ብዙ ጥቅስ አገኘሁ - ከቅዱስ መጽሐፍህ - ገልጬ አይቼ
ከራሴ ላይ ብቻ - አንድ ጥቅስ አጣሁኝ - በበደል ተኝቼ
ውጤቴ ደካማ - ትምህርት የማይሠርጸኝ - ተማሪ ብሆንም
ይህችን ዓመት ተወኝ - ደግሞ ትንሽ ልማር - ታገሠኝ አሁንም!

እባክህ አልቆረጥ - በቅዱስ መሬትህ - ልቆይ ፍቀድልኝ
ያፈሩት ቅዱሳን - የፍሬያቸው ሽታ - መዓዛ እንዲደርሰኝ
የተሸከምከኝ ሆይ - ዛሬም ተሸከመኝ - አትሰልቸኝ አደራ
ማን ይታገሠኛል - ጠላት እየሆንኩት - አይሠሩ ስሠራ!
አታውጣኝ ከቤትህ - ብዙ ቦታ አልይዝም - ፍሬ ስለሌለኝ
ስፍራ የማያሻኝ - ቤት የማላጣብብ - ፍሬ አልባ በለስ ነኝ!
ቦታስ የሚይዙት - ባለ ምግባሮቹ - ቅዱሳንህ ናቸው
ልክ እንደ ዘንባባ - የተንዠረገገ - ተጋድሎ ጽድቃቸው!
ከሊባኖስ ዝግባ - እጅጉን የበዛ - ገድል ትሩፋታቸው!
እኔ አይደለሁም - ቦታስ የምትይዘው - የአንተው እናት ናት
ሥሮቿ በምድር - ጫፎቿ በሰማይ - ሲደርሱ ያየናት
ይሀችን ዓመት ተወኝ - ከሥርዋ እሆናለሁ - ባፈራ ምናልባት!..
ይህችን ዓመት ተወኝ - እባክህ አምላኬ - አንድ ዓመት ምንህ ናት
ሺህ ዓመት አንድ ቀን - አይደለም ወይ ለአንተ - ዓመት ኢምንት ናት!
ይሄ ዓመት አልፎ - ዳግም ‹ዓመት ሥጠኝ› - እስከምልህ ድረስ
እባክህን ጌታ - ይህችን ዓመት ተወኝ - የወጉን እንዳደርስ!

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ

---
ምንኩስና የተጀመረው እንዴት ነበር? ከመጽሐፍ ቅዱሳዊ መነሻዎቹ ባሻገር የምንኩስናን ታሪክ ስናጠና በ4ኛው ክፍለ ዘመን እንደተጀመረ ይታወቃል:: ለሦስት መቶ ዓመታት በአሰቃቂው ዘመነ ሰማዕታት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መከራ ስትቀበል ክርስቲያኖችም በየቀኑ ሲገደሉ የነበረበት ዘመን ድንገት አበቃ:: በደማቸው ለመጠመቅና በሞታቸው ክብር ለመቀዳጀት የተዘጋጁ ምእመናንን ድንገት "በቃ ከእንግዲህ አትሞቱም" የሚል አዋጅ ታወጀባቸው::

ዕረፍት አገኘን ብለው የተደሰቱ እንደነበሩ ሁሉ ለሰማዕትነት ቆርጠው ለክብር አክሊል ተዘጋጅተው የነበሩ ብዙዎች ግን ድንገት ሰማዕትነት ሲቆም አዘኑ:: ከሰማዕትነት ክብር ወርደው እንደማንኛውም ሰው መኖር ከበዳቸው:: ስለዚህም በሰይፍ ባይሞቱም በፈቃዳቸው ሞተው ለክርስቶስ ሕያው ሆነው ሊኖሩ ወደ ገዳማዊ ሕይወት ወደ ምንኩስና ጎረፉ:: ይህም ክስተት ለምንኩስናና ለገዳማዊ ሕይወት ምክንያት ሆነ::

ዝቋላን በመሳሰሉ ገዳማት የሚገኙ መነኮሳት በሥጋ የሚሞቱበት ቀን ሳይደርስ በክርስቶስ ፍቅር በፈቃዳቸው የሞቱ ሐዋርያው እንዳለው "ሥጋን ከክፉ ምኞቱና መሻቱ ጋር የሰቀሉት" ናቸው:: ሰማዕትነትም ቀድመው የተመኙት ክብር ነበር:: በእነርሱ መገደል የሞትነው በእነርሱ ጸሎት ብርሃንነት የምንኖር ፣ ስንጨነቅ ከእግራቸው ሥር የምናለቅስ ፣ በዓለም ማዕበል ስንላተም በመስቀላቸው መልሕቅ ወደ ጸጥታ ወደብ የምንደርስ እኛው ነን::

ባለቆቡ ሰማዕት አባቴ ሆይ እርስዎን የገደሉ የገደሉት የእኔን ተስፋ ነው:: ሰማዕቱ መነኩሴ ሆይ በእርስዎ ሞት የተቀደደው የዕንባዬ መሐረብ ነው:: አንጀታችን በኀዘን እርር የሚለው ለእናንተ ሳይሆን ለራሳችን ነው:: ከእናንተ ጸሎት በቀር ምርኩዝ የሌለን እኛ ይለቀስልን እንጂ ለእናንተ አናለቅስም:: ቀድማችሁ የጠላችኋት ዓለም ብትጠላችሁ አይገርምም:: በፍቅርዋ ለተሸነፍን ለእኛ ግን ዕንባ ያስፈልገናል:: እውነተኛዋ ቤተ ክርስቲያን የትኛዋ እንደሆነች ፣ ዘመነ ሰማዕታትን የምትደግመዋ የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ማን እንደሆነች በደማችሁ ያሳያችሁ ምስክሮች ሆይ ለእኛ እንጂ ለእናንተ አናለቅስም:: የእኛን እግር ከማጠብ ፣ የእኛን ብሶት ከመስማት ፣ የእኛን የክርስትና ስም ዘወትር በጸሎት ከመጥራት ፣ እኛን ተቀብሎ ከማስተናገድ አረፍ ብላችሁ ከመነኮሳችሁለት አምላክ ዕቅፍ ስለገባችሁ አናዝንም:: የምናዝነው በተራራ ላይ ያለ መብራታችን ለጠፋብን ለእኛ ነው:: የእኛ ደብረ ታቦር ዝቋላ ሥሉስ ቅዱስ በደመና ይጋርድሽ እንጂ ምን እንላለን?

ገዳምንና ገዳማውያንን መንካት የንቡን ቀፎ ማፍረስ ነው:: ቤተ ክርስቲያን ከቅዱስ ሲኖዶስ እስከ ዐቃቢት ያሉት ሁሉ በገዳም ቀፎነት የተሠሩ የማር እንጀራዎች ናቸው:: ማሩን የሚጋግሩት ንቦች ያሉት ከቀፎው ገዳም ውስጥ ነው:: የአቡየ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የቆብ ልጆች በአስኬማ ላይ የሰማዕትነት አክሊል የደረባችሁ ቅዱሳን መነኮሳት ጸልዩልን በዙፋኑ ፊት ቆማችሁ "ቅዱስና እውነተኛ ጌታ ሆይ፥ እስከ መቼ ድረስ አትፈርድም ደማችንንስ በምድር በሚኖሩት ላይ እስከ መቼ አትበቀልም?" ብላችሁ ስለ እኛ አማልዱ:: (ራእ. 6:10)
ቅትለተ መነኮሳት ከዝቋላ ወደ ደቡብ አፍሪቃ

አባ ተክለ ሃይማኖት (አባ ተክላ) ደቡብ አፍሪቃ ገጠር ውስጥ የሚያገለግሉ መነኩሴ ነበሩ:: ወላጆቻቸው ለኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ምልጃቸውን በመማጸን ተስለው ስለወለዱአቸው ስማቸውን በጻድቁ ስም ሰይመዋቸዋል:: ከባለጸጋ ቤተሰብ የተወለዱትና የሚተዳደሩበት የራሳቸው መርከብ የነበራቸው እኚህ ወጣት የእንጦንስ የመቃርስን መንገድ ተከትለው ሀብታቸውን ሸጠው ለድኆች ሠጥተው የቀረውን ለገዳም አውርሰው መነኮሱ:: ከዓመታት በፊት በገዳማቸው ተገኝቼ በረከት በተቀበልሁበት ወቅት እንዴት እንደመነኮሱ ፣ ለአቡነ ተክለ ሃይማኖት ያላቸውን ፍቅርና አንዳንድ ነገሮችን አጫውተውኝ ነበር:: ለእኔም ያሳዩት ስስትና ፍቅር ከሕሊናዬ የማይጠፋ ነው:: ዛሬ በግፍ ሰማዕትነትን እንደተቀበሉ ቢቢሲ ዘግቦ አየሁ:: ሰይጣን የእውነተኛይቱን ቤተ ክርስቲያን አድራሻ መቼም አይሳሳትም::

በግብፃዊው ጻድቅ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ስም በተሰየመ ገዳም የመነኮሱ ኢትዮጵያውያን ሰማዕታት በሆኑ በሳምንቱ በኢትዮጵያዊው ጻድቅ ተክለ ሃይማኖት ስም የተሰየሙ መነኩሴ ከወንድሞቻቸው ጋር ሰማዕትነት ተቀበሉ:: ሰይጣን ከሃይማኖታችን እንጂ ከዘራችን ጠብ የለውም::

ሰአሉ ለነ አስተምሕሩ ለነ
እስመ በጸሎተ ጻድቅ ትድኅን ሀገር

“በዚያን ጊዜ ለመከራ አሳልፈው ይሰጡአችኋል ይገድሉአችሁማል፥ ስለ ስሜም በአሕዛብ ሁሉ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ" ማቴ. 24:9

https://www.facebook.com/share/U25yhRDtJaBojkjB/?mibextid=WC7FNe
2024/03/29 10:44:58
Back to Top
HTML Embed Code: